yegizewkal
ቃልህ ተገኝቶአል እኔም በልቼዋለሁ አቤቱ፥ የሠራዊት አምላክ ሆይ፥ በስምህ ተጠርቻለሁና ቃልህ ሐሤትና የልብ ደስታ ሆነኝ። ትንቢተ ኤርምያስ 15፥16

  • Home/መነሻ ገጽ
  • Gospel Thoughts/የወንጌል አስተምህሮ
    • ነገረ ድነት/Salvation
  • The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ
    • Literature/ስነ-ጽሑፍ
    • ከመጽሐፍት ዓለም
  • Churches/ቤተ ክርስቲያን
    • Religious News/ሐይማኖታዊ ዜና
  • Testimony/ምስክርነት
  • ማስታወቂያ/Advertisement
  1. You are here:  
  2. Home
  3. Gospel Thoughts/የወንጌል አስተምህሮ

Gospel Thoughts/የወንጌል አስተምህሮ

እስክንድሮሶች

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

እስክንድሮሶች


የእውነት እና የሐቅ ተፃራሪዎች፣ በሐሳብ ሙግት ሳይሆን የሚጠሉትን በያዙት አቋምና እምነት የማይሟገቱ፣ ይልቁኑ በተቃውሞና በማጥላላት ላይ ተጠንዘው የሚገኙ፣ እውነትን እድሜ ሚያሳጥሩ የመሰላቸው፣ የሚቃወሙትን ግን እያጠነከሩት እንደሆነ የማይገባቸው፣ የራሳቸውን በአግባቡ ሳያውቁ የሌላውን እውነት ለማደብዘዝ፣ አዚም የሚያደርግ ባልጠፋበት #የዘመኑ_አዚመኞች፣ ግን ሳያውቁት ሌላውን እያጠነከሩ ያሉ #የዘመኑ_አስክንድሮሶች መኖራቸውን ለቅፅበት መዘንጋት የለብንም። ከሚቃወሙ የሚያነጥሩት ነሐስ አዋጪ መሆኑን ቢረዱ ምን ያህል መልካም ነበር? ምን ያህል ትርፋማ ይሆኑ ነበር። በተለይ የወንጌልን እውነት ይዘው እና አንግበው የሚንቀሳቀሱትን፣ በዘመኑ ላይ እየሆነ ያለውን ኢ-መፅሐፍ ቅዱሳዊ አስተምሮቶችን ነቅሰው በማውጣት እውነታውን ፍንትው አድርገው ገልጠው እና ገልጸው የሚያስተምሩትን በትችት ናዳ ለማሸማቀቅ የሚታትሩ #የዘመኑ_አዚሞች_አዚመኞች እነ #እስክንድሮስ እንዳሉ መረዳቱ እጅግ ጠቃሚ ነው። 
“የናስ አንጥረኛው እስክንድሮስ እጅግ ከፋብኝ፤ ጌታ እንደ ሥራው ይመልስለታል።” — 2ኛ ጢሞቴዎስ 4፥14።
የእግዚአብሔርን እውነት ይዘው እውነት እንድትታይ ሌት ተቀን ለምትታትሩ የእውነት ታጋዮች የሙግት ጊዜ ባይኖረን ግን እውነትን በፍቅር በመያዝ እና እየገለጥን መኖሩ ተገቢ ቢሆንም #ከእስክድሮስ መጠበቁ ግን እጅግ ጠቃሚ ነው። #እስክንድሮስ ከተቃውሞ ውጭ እንደማይሆን ማወቁም ተገቢ ነው። “አንተም ደግሞ ከእርሱ ተጠበቅ፥ የምንናገረውን እጅግ ተቃውሞአልና።”— 2ኛ ጢሞቴዎስ 4፥15። 

#የእነ_እስክድሮስ አቅማቸውም አቋማቸውም ተቃውሞ መሆኑ ሳይዘነጋ የተሰጠንን ሥራችንን እየሠራን መቀጠሉ እርሱ ዋናው ነገር ሲሆን ቦታም አለመስጠቱ እጅግ ተገቢ ነው። #እስክንድሮስ ጊዜን አባካኝ መሆኑን አለመርሳቱ ተገቢ ነው። ክርክር ጊዜና ዕድል መስጠት መሆኑን ለአፍታ_ለቅፅበት መዘንጋት የለብንም። ሥራው የተማርነውን እና የምናስተምረውን ትምህርት እግር በእግር የሚቃወም መሆኑን መዘንጋት የለብንም።
“ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ እናንተ የተማራችሁትን ትምህርት የሚቃወሙትን መለያየትንና ማሰናከያን የሚያደርጉትን ሰዎች እንድትመለከቱ እለምናችኋለሁ፥ ከእነርሱ ዘንድ ፈቀቅ በሉ፤” — ሮሜ 16፥17።

#እነ_እስክንሮስ በክርስቶስ ትምህርት የማይኖሩ አምላክ የሌላቸው መሆኑን ማወቁ ተገቢ ነው፣ ተቃውሞአቸውም ይህ ነው። በክርስቶስ ትምህርት ኖረው አምላክ ያላቸውን በማሳት የተካኑ መሆናቸውን ማወቁ ተገቢ እና ወሳኝ ነገር ነው። 

መፍትሄው
1-
መጠበቅ
2-
ፈቀቅ ማለቱ ተገቢ ነው።

ሰናይ አገልግሎት እና ዘመን ይሁንልን!

ወንድም በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

ዲዮጥራጢስ

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

ዲዮጥራጢስ


በመልዕክተኛው በዮሐንስ ዘመን በቤተክርስቲያን የነበረ ዋነኛ ሆኖ መታየትን የሚፈልግ፣ የእውነትና የእውቀት ጠላት የሆነ፣ እውነትን ይዘው ለሚጓዙ ዕንቅፋት፣ እውነትን አንግበው ለሚፈጥኑ ትክል ድንጋይ፣ ለቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ግድ የሌለው፣ ዳሩ ግን ዋናቸው ሊሆን የሚወድ የስልጣን ጥመኛ፣ እውነትን አንግበው የሚሄዱትን የማይቀበል፣ የመጣውን በክፉ ቃል በመለፍለፍ የሚነቅፍ (ያልተጎሰመ_አንደበት_አንጋቢ)፣ ለወንድሞች ቦታ የሌለው፣ የማይቀበል፣  ሌሎችን በማሳመፅ እውነትን የያዙትን እንዳይቀበሉ የሚያደርግ፣ ከትዕዛዙ የወጣውን ከቤተክርስቲያን የሚያስወጣ፣ የሚያሸሽ ዛሬም በአጠገባችን፣ በዙሪያችን ያሉ አይደሉምን?

ለጋይዮስ እና ለድሜጥሮስ፦ በመልካም የሚሄዱትን፣ በሁሉ ዘንድ በመልካምነት የሚመሰከርላቸው አጠገብ የማይጠፋ ድዮጥራጢስ፣ ዛሬስ የሉምን? እጅግ በቁጥር በዝተው፣ ከፍታውን ይዘው፣ ከጨለማው አለም ሰራተኞች በላይ ተግተው የሚሠሩ ዛሬም አሉ። ስውር ሥራ፣ ስውር ደባን እንደ አዳኝ አድፍጠው የሚከውኑ፣ ሁሉን ተቆናጥጠው የሚሠሩ ዛሬም አሉ። ርቀው የማይሄዱ የወዳጅ ጠላት እነ አኪጦፌል ዛሬም አሉ። የጥንቱ አኪጦፌል መልኩን ቀይሮ የመጣ ዲዮጥራጢስ እሱ ሳይሆን ይቀር? የድሮ ሰይጣን ዛሬም እሱ ነው። የተሸነፈ ግን ነው!

እነ ዲዮጥራጢስን እንጠንቀቃቸው። ሁሌም አጠገባችን አይታጡም። ትንሿን መልካም ነገር እንዳንሰራ ነገሮችን ያበላሻሉ፣ ያጠፉብናልም።

ይህን ማወቅ እና መረዳት ይሁንልን

“ሥራ የሞላበት ትልቅ በር ተከፍቶልኛልና ተቃዋሚዎችም ብዙ ናቸው።”— 1ኛ ቆሮንቶስ 16፥9።
“
በአንድም ነገር እንኳ  በተቃዋሚዎች_አትደንግጡ፤ ይህም ለእነርሱ የጥፋት፥ ለእናንተ ግን የመዳን ምልክት ነው፥ ይህም ከእግዚአብሔር ነው፤” — ፊልጵስዩስ 1፥28።

ዲዮጥራጢስ ድጡ ለአንተ!

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደሙ ይሰውረን!

ወንድም በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

የተፅእኖ ሰው

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

የተፅእኖ ሰው

እነርሱ በእምነት መንግስታትን ድል ነሡ ጽድቅን አደረጉ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ

                                                       ዕብራውያን 11፡33

በምድራችን ላይ በየትኛውም ዘመን በታሪክ መዛግብት እና በአፈ ታሪክ እንደሚነገረን፣ ከኖርንባቸው ዘመናት ቀድመው የኖሩ በፍልስፍናቸው አመለካከት ይሁን፣ በÞለቲካ አመለካከታቸውና ፍልስፍናቸው ይሁን፣ በፈጠራ ሥራና ግኝት ልህቀት ይሁን፣ ብቻ በተሰማሩበት በየትኛውም ዘርፍ ተፅዕኖን ፈጥረው ለዓለም የሚጠቅም አዎንታዊ ይሁን፣ የማይጠቅም አሉታዊ ጉዳይ ይሁን ሰርተው አልፈዋል፣ አንቱታንም ተችረው፣ ተሞግሰው ለበጎ ነገር ይሁን ለዕኩይ አንድ አሻራ ጥለው አልፈዋል፡፡

በክርስትና እምነት መፅሐፍ ቅዱሳችን እንደሚነግረን በምድር ላይ ተፅዕኖን ፈጥረው የኖሩ ሰዎች እጅግ ብዙዎች ሲሆኑ ተፅዕኖ ብቻም አይደልም ተፅዕኖ ፈጥረው የኖሩበትን አሳይተውና ገልፀው፣ አስከብረው  ኖረው አልፈዋል፡፡

የሰው ልጅ በዘመኑ በተለይ በኖረበት ዘመን ባለበት አካባቢ አንድ የማይረሳ አሻራን ጥሎ ማለፍ የግድ ነው፡፡ ይህም ሲባል ከላይ በአለም ካሉ ሰዎች ዘንድ በተነገረ የተፅዕኖ ሰውነት ዝርዝር ቢታይም በእኛ እግዚአብሔርን እናመልካለን በምንል እና ክርስቲያኖች ነን ብለን እራሳችንን የለየንና ሌሎችም የሚያውቁን በዘመናችን እንደ ቀደሙት አባቶች በዘመናችንና በኖርንባቸው ማህበረሰቦች ዘንድ እንደ ቀደሙት የእምነት አባቶች አንድ ተፅዕኖ ፈጥረን የፈጠርንበትንም አሳይተን፣ አሳውቀን ማለፍ የግድ ነው፡፡

በተለይ በዚህ ዘመን ያለን የወንጌል አማኞች ነን ብለን የምንናገር፣ በሌሎችም ዘንድ እሱ እኮ፣ እሷ እኮ ክርስቲያን ነች፣ አማኝ ነው ተብለን ምንታወቅ በተቃራኒው ግን በሌላ መልክ የምንታወቅ ብዙዎች ነን፡፡ ለያዝነው ወንጌል እውነት እንደሚገባ የማንኖር፣ የኖረውንም የምናስተች እጅግ አያሌ ሰዎች መሆናችን የገሃዱ አለም ሃቅ ነው፡፡ ሊያገለግሉ ለቆረጡ ሰዎች የመሰናክል እና የእንቅፋት ድንጋይ በመሆን ለአለም እና ለሰይጣን መንግስት ደጋፊ ሃሰብ አቅራቢዎች መሆናችን እጅግ ለእግዚአብሔር መንግስት ሳንካዎች ሆነናል፡፡

የእግዚአብሔር ልጅ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዋጋ የከፈለበትን ትልቁን የክርስትና እምነታችን በጥቂቶች አይደልም፣ በበዙቱ ስህተት ሲተች፣ ሲነቀፍ ይታያል፡፡ የቀደሙት የወንጌል አርበኞች የረሳቸውን ጥቅምና ዝና ትተው ወደ ኋላ አድረግው አይበልጥብንም የራሳችን ጉዳየው በማለት ዋጋ ከፍለውበት፣ እምቢ አሸፈረኝ ሰውን አንሰማም የሰማዩን እግዚአብሔር ብቻ ሰምተን ነው ምናገለግለው ብለው ዘመናቸውን የሰጡበትን፣ መንግስታትን እምቢ ማለታቸው ለወንጌሉ እውነትና ሀቅ ላመኑበት ይህ ነው ማይባል እና የማይገመት ዋጋ ከፍለው ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስ አስከብረው አልፈዋል፣ ማለፍ ብቻ አይደለም የማይሻርና የማይረሳ ተፅዕኖን ፈጥረው አልፈዋል፡፡

የተፅዕኖ ሰዎች

1.  በራሳቸው ላይ ወስነው የወጡ ናቸው- ሙሴ

የአርባ አመት የምቾትና የድሎት ዘመንን እምቢኝ ይበቃኛል በማለትና ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራን መርጦ፣ ብድራቱንም ትኩር ብሎ በመመልከት ወስኖ መውጣቱና የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ ከኮሬብ ተራራ ጀምሮ በመቀበል፣ እግዚአብሔር ወደ ፈርኦን ቤት ልኮት በእግዚአብሔር ላይ በመታመን፣ ድምፁን ተቀብሎ እግዚአብሔር እንዲህ ይልሃል ያገለግለኝ ዘንድ ሕዝቤን ልቀቅ ይልሃል የሚለውን መልዕክት በመያዝ መውጣቱ በእግዚአብሔር ላይ ያለው የፀና እምነቱ የንጉስን ቤት ባለመፍራት በእግዚአብሔር ላይ ያለው እምነቱ ንጉስን እጅ እስከሚያሰጥ ድረስ አድርሷል፡፡

ማንነቱን ሲያውቅና ሲገባው፣ የራሱ ወገን ያልሆነን ሲረዳ፣ የራስ ሃገር እንዳልሆነ፣ የኪዳንና የአባቶቹ መሬትና ሃገር እንዳልሆነ ሲገባው፣ ዝርያው ከዛ እንደማይመዘዝ ሲያውቅ የራሱን ህዝብ በእግዚአብሔር ምሪት ነፃ ሊያወጣ የቻለ፣ በእግዚአብሔር ላይ በመታመን የተፅዕኖ ሰው በመሆን ትልቅ የእግዚአብሔርን ሥራ ሰርቶ ትውልድን ወደ ኪዳን ምድር መርቷል፡፡

2.  ጊዜያቸውን በአግባቡ የተጠቀሙ ናቸው- ዳዊት

ዳዊት የልጅነት ሕይወቱ በምድረ በዳ ቢያሳልፍም እግዚአብሔር በዛ ቦታ የወደፊት ኑሮውን በሚገባ ያሰልጠነበት፣ ያስተማረበት፣ ብቁ እሰከሚሆን እና እግዚአብሔር ለራሱ አላማ እስኪጠራው ድረስ የቆየበትና የከረመበት ስፍራ ምድረበዳ ነው፡፡ በተለይ ከድብና ከአንበሳ ጋር በመታገል በጎቹን ሲያስጥል የሰለጠነበት መንገድ የወደፊቱን የሕዝብን ኃላፊነት፣ የሐገር ጉዳይን በኃላፊነት፣ የእምነቱን ጉዳይ እንዴት ከጠላትና ከባዕድ አካላት እንደሚጠብቅ ጭምር እግዚአብሔር ያሰለጠነበት መንገድ እጅገ አስገራሚ ነው፡፡ ከአባቱ በጎች ጥበቃ የተጀመረ ሕይወቱ፣ ለራስ ሳይሆን ለሌላ ወይም ለቤተሰቡ መኖሩ እንዴት ለሌላ መኖር እንደሚቻል ጭምር በሚገባ አሰልጥኖታል፡፡

ከዚህ ባለፈ ዳዊት በእግዚአብሔር ጥሪ መሰረት ለዓላማው ሲጠራው ዘመኑን በሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠትና ሃሳቡንም በማገልገል ዘመኑን ሰጥቶታል፡፡ በተለይ የልጅነት የምድረበዳ ህይወቱን ቀጥታ እግዚአብሔር በመጠቀም ዕድሜውን በሙሉ የእግዚአብሔርን ጦርነት ተዋግቶ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ከባዕዳን ሰዎችን  ነፃ በማውጣት እና እምነትንም በመጠበቅ በዘመኑ ሁሉ በድል ተመላልሷል፡፡ 

በተለይ ዳዊት ከሚለይባቸው ባህሪያት መካከል በየትኛውም ጦርነት እግዚአብሔርን ሳይጠይቅ የወጣበት ጦርነት የለም፡፡ እግዚአብሔርም ዳዊት በሔደበት ሁሉ ድልን ይሰጠው ነበር ሕዝብም በማሞገስና በመሸለል ውዳሴን ሲያቀርቡለት ነበር፡፡

ዳዊት መጠየቁ እግዚአብሔር ዋስትና እንዲወስድለትና እርግጠኛም ለመሆን እግዚአብሔርን አምኖ በመጠየቅ ይወጣ ነበር፡፡ የእግዚአብሔርን ሥራ በራስ እንደማይሰራ ዳዊት ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ የተፅዕኖ ሰው ማለት ተፅዕኖ እንዲያደርግ የሚያደርገውን እና የሚረዳውን ማወቅ ማለት ነው፡፡

3.  በዘመናቸው ላይ ተፅዕኖ ፈጥረው አልፈዋል

በመፅሐፍ ቅዱሳችን በቀደሙት አባቶች ዘንድ ገንኖ እና በዋናነት ይታይ የነበረው በእግዚአብሔርና በእግዚአብሔር ጉዳይ ላይ የማይደራደሩበት ነገር ትልቁና ዋነኛው በሕይወታቸው የሚታየው ነው፡፡ በተለይ በተፃራሪ መንገድ የእግዚአብሔርን ነገር በመቃረን የሚመጡትን በምንም አይነት መንገድና መልኩ አይታገሱበትም፣ በተቃራኒ በመቆም በእግዚአብሔር በመወራረድ በዘመናቸው ላይ የመጣውን ተግዳሮት ፊት ለፊት በመጋፈጥ ሲያጠፉትና ሲያስወግዱት ታይተዋል፡፡

ከሚገርመው ነገር አንዱ ብቸኛ መሆናቸውን ጨርሶ አያስቡትም፡፡ ከእኔ ጋር ያለው ከሁሉም ይበልጣል ማለት የየዕለት መርሃቸውና የእምነት መግለጫቸው ሲሆን በእግዚአብሔር ከአሸናፊዎች መብለጣቸው ትልቁ መፈክራቸውም ነው፡፡ 1ኛ ነገሥት 16፡31-33 የአክዓብን ታሪክና የኤልያስን ታሪክ በምንመለከትብት ጊዜ በተለይ አክዓብ በኪዳን ምድር ኢዮርብዓም በሄደበት ኃጢአት ሄዶ በተለይም ኤልዛቤልን ማግባቱ እና የበዓል ነቢያትን በገበታዋ መመገብዋ እና አክዐብን ማሳቷ ኤልያስ ሚጣገሰው ጉዳይ ባለመሆኑ በምድሪቱ ምንም አይነት ጠልና ዝናብ እንዳይዘንብ ማድረጉና እግዚአብሔር ሸሽጎት ሲመግበው ምን ያህል በዘመኑ ላይ በእግዚአብሔር ታምኖ ተፅዕኖ ማድረጉና እግዚአብሔር አስከብሮ ተፅእኖ ፈጠሯል፡፡

4.  ከራሳቸው በላይ ላመኑበት ኖረዋል

በተለይ ባመኑበትና በተማሩት የአባቶች መንገድ በተሰጣቸውም በህገ እግዚአብሔር ወደ ግራም ወደ ቀኝም ሳይሉ በእግዚአብሔር ሕግ መኖራቸው እግዚአብሔር እራሱ ከእነርሱ ጋር መሆኑን በትክክል አሳይቷል፡፡ በእግዚአብሔር ሕግ የሄዱ እና የኖሩ፣ ብሎም መንገዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር ያደረጉ በምንም አይነት መንገድ ውስጥ ሲያለፉም ይሁን በፈተና ውስጥ ሲያልፉ እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር ነበረ በድልም አልፈው በዘመናቸው ተፅዕኖን ፈጥረው እግዚአብሔርን ለሕዝብ አሳይተው የእነርሱ አምላክ በሀገር ይመለክ አሰኝተው አልፈዋል፡፡

በምርኮ የነበሩትና የንጉስ አርጤክስስ ሚስት በነበረችው በአስቴር ዘመን በህገ እግዚአብሔር በመመራት የኖሩትን አይሁድ ሓማ ሊያሰገድል በተሰናዳበትና ዝግጅቱን ባጠናቀቀበት ዘመን ንግስቲቱ የፆምና የፀሎት ጊዜን ለአይሁድ ማወጇ እና ወደ እግዚአብሔር መጮኋ ትልቅን የድል ብስራትን ማምጣቱና የታወጀውን አዋጅ ማስገልበጧ ሁሉን መቀየር ወደ ሚችለው ፊቷን ከህዘቧ ጋር ማዞሯ መልስን ከእግዚአብሔር አምጥቶላቸዋል፡፡ በመቶሃያ አገራት የአይሁድ አምላክ ይመለክ እንዲሉ ማድረጋቸው አንደኛው በእግዚአብሔር ላይ መተማመናቸውና ፀሎትን ሰምቶ ወደ ሚመልሰው መጮሃቸው ያመጣው ድልና የተፅዕኖ ሰው አድርጓቸዋል፡፡

በኃጢአት ላይ ባለ አመላካከት እጅግ የጸና አቋም በመያዝና ከእግዚአብሔር ጋር መልካም ግንኙነት፣ እግዚአብሔርን ማስቀደሙ ምንም እንኳን ፀሎት እንዳያደርግ በአዋጅ ቢከለከልም እግዚአብሔርን ማለቱ የዕለት ተግባሩ እና የማቋረጥ መሆኑ የገባው ዳንኤል በዘመኑ ላይ ተጽዕኖን በማምጣት እግዚአብሔር በምድር በመቶ ሃያ ሀገራት ላይ እንዲመለክ አድርጓል፡፡ በእግዚአብሔር ላይ መታመኑ ከአናብስት አፍ እግዚአብሔር ሲያድነው ሃገር ምድሩ ቢመለከትም ለዳንኤል ሲል ንጉሱ እንቅልፍ ማጣቱ ምን ያህል እግዚአብሔር ለዳንኤል እንደሚጨነቅለት አስረጂ ነው፡፡

እኛስ ዛሬ በዚህ ዘመን ያለን ክርስቲያኖች በእርግጥ በእግዚአብሔር ህግና ትዕዛዝ የእነርሱን ፈለግና አብነት ተከትለን ይሆን እየኖርን ያለነው?

5.  ለጥቅማቸው ሳይሆን ላመኑበት ጥቅም ኖረዋል- ደቀመዛሙርት ሁሉን ትተው

በሰው አሰራር የተጠሩበት ስፍራ በምንም መልኩ ለመመረጥ መስፈርት እና ቅድመ ሁኔታ ሊሆን ከማይችልበት ስፍራ የተጠሩት ደቀ መዛሙርት፣ ለጥሪው አፋጣኝ መልስ በመስጠት የተከተሉት፣ የያዙትና የነበራቸውን ነገር በመተው ጌታን ተከትለውታል፡፡ የሶሰት አመት ተኩል ከጌታችን ኢየሱስ ጋር መቆየታቸው ሊሰራቸውና ለአገልግሎት ሲያዘጋጃቸው ምን ያህል እግዚአብሔርን ማገልገል እንዳለባቸውም ጭምር አሰልጥኖአቸዋል፡፡ መሄድ ካስፈላጋቸው እንኳን ሲጠይቃቸው ከአንተ ወዴጥ እንሄዳለን አንተ የህይወት ቃል አለህ፣ ሁሉን ትተን ተከትለንሃል በማለት የቁርጠኝንትንና የውሳነየ ሃሳባቸውን ገልፀው የቀጠሉ፣ በአገልግሎት በዘመናቸውም ትልልቅ ተግዳሮትን ቢያልፉም ባሰለፋቸው እግዚአብሔር ላይ በመታመን፣ ምንም ማንንም ሳይፈሩ እኛ ግን የተሰቀለውን ክርሰቶስን እንሰብካለን፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትናም ዛሬም እሰከ ዘላለም ያው ነው በማለት ተፅዕኖን በወንጌል ኃይል በዘመናቸው ላይ ፈጥረው አልፈዋል፡፡

ዛርስ እኛ ክርስቶስን እንከተላለን የምንል በዘመናችን ላይ ክርስቶስን በመያዝ ጠፀዕኖን እየፈጠርን ነን?

6.  በእምነታቸው ተቃራኒ ከሆኑት ጋር ፊት ለፊት ተጋፍጠዋል

በነቢያት ዘመን ነቢያት ከሚያደርጓቸው አብይ ጉዳዮች መካከል በተለይ እግዚአብሔር ከሚጠላቸው ነገሮች ጋር አለመተባበር ሳይሆን ፈፅመው እነዚያን ነገሮች ከኪዳን ምድር ማጥፋታቸው ትልቁ ስራቸው ነበር፡፡ በምድራቸው እግዚአብሔር ብቻ እንዲመለክ፣ ሕገ እግዚአብሔር ብቻ በሕዝቡ ዘንድ እንደሚገባ እንዲተገበር ማድረጋቸው ከብዙ ስራዎጫቸው መካከል የሚጠቀስ ነው፡፡ በተለይ ኤልያስና የበዓል ነቢያት ያደረጉት ስራ እጅግ የሚገርም ነው፣ በተለይ ውርርዳቸው በአምለካቸው ላይ በመተማመን የሰሩት ስራ፣ የማን አምላክ ይበልጣል ብለው መፎካከራቸው፣ ኤልያስ በእግዚአብሔር ላይ ያለው መታመንና ንጉሱን ፈልጎ መገናኘቱ፣ ይባስ ብሎ የበዓል ነቢያት አራት መቶ ሓምሳውን መጥራቱ፣ የመሰዊያን ነቢያት አራት መቶውን መጥራቱ እና ከነዚህ ስምንት መቶ ሃምሳው ለባቻው ከአግዚአብሔር ጋር መጋፈጡ የሚያስገርምና በድል መመለሱ ትልቅ እምነቱ ነው፡፡

የእስራኤል መንግሥት በውሃ እጦት መቸገሩን ቀጠለ። ንጉስ አክዓብ ህዝቡ በኣል የሚባለውን የሀሰት አምላክ እንዲከተሉ ነገራቸው።1 ነገስት 18፥1–2፣ 17–18

እግዚአብሔር ነቢዩ ኤልያስ ከአክዓብ ጋር እንዲገናኝ ላከው። ኤልያስ ህዝቡን በሙሉ ወደ ተራራው ጫፍ እንዲመጡ ጋበዛቸው። እርሱም እግዚአብሔር እና ከበአል የትኛው እውነተኛ አምላክ እንደሆነ እንዲያዩ ንጉሱን እና ነቢያቱን ወደ ፉክክሩ ጋበዛቸው። 1ኛ ነገሥት 18፡19–21

ኤልያስ ፉክክሩን ገለጸ። እርሱ እና ካህናት ወይፈን በመሰዊያ ላይ ይሰዋሉ፣ ነገር ግን ራሳቸው እሳትን አያነዱም። ይልቁንም ካህናቱ እሳት ይለኩስ ዘንድ ወደ በኣል ይጸልያሉ። ከዚያም ኤልያስ እሳት ይለኩስ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ይጸልያል። ኤልያስ እውነተኛ አምላክ ብቻ እሳቱን እንደሚለኩስ ያውቅ ነበር።1ኛ ነገሥት 18፡22–25

 

የበኣል ካህናት ወደ አምላካቸው ከጠዋት እስከ ከሰዓት በኋላ ጸለዩ፣ ነገር ግን ምንም አልደረሰም። ኤልያስ ቀለደባቸው እናም አምላካቸው በኣል ተኝቶ ይሆናል አለ። 1ኛ ነገሥት 18፥26–27፡፡ ነቢያቱ ተናደዱ፣ በመሰዊያውም ላይ ዘለሉ፣ እናም እስከ ምሽት ፀለዩ። አምላካቸው መልስ ይሰጣል ብለው ተስፋ ነበራቸው፣ ነገር ግን ምንም እሳት አልነበረም። 1ኛ ነገሥት 18፥28–29፡፡ ከዚያም የኤልያስ ተራ ነበር። የጌታን መሰዊያ አበጀ፣ በመሰዊያውም ዙሪያ ጉድጓድ ቆፈረ፣ እንዲሁም መስዋዕቱን አዘጋጀ።1ኛ ነገሥት 18፥30–32

 

Description: ኤልያስ እና ህዝቡ መሰዊያ ሲገነቡ

 

ኤልያስ ሕዝቡ ጉድጓዱን ውሃ እንዲሞሉ እና በመሠዊያው እርጥብ እንጨት ላይ ለሦስት ጊዜ እንዲያፈስሱ ጠየቃቸው። ውሀው እንጨቱን እና መሰዊያውን አረጠበ። ጉድጓዱንም ሁሉ ሞላ። 1ኛ ነገሥት 18፥33–37

 

Description: ኤልያስ በመሰዊያው አጠገብ ሲጸልይ

 

ኤልያስ እውነተኛውን የእግዚአብሔርን ሀይል እንዲያሳይ ወደ ጌታ ጸለየ። የጌታ እሳት ወረደች እናም መስዋዕቱን፣ እንጨቱን፣ ድንጋዮቹን፣ እና ውሀውን በላች። ህዝቡም የኤልያስ አምላክ እውነተኛ እግዚአብሔር እንደሆነ አወቁ። ኤልያስ ድርቁ እንዲያበቃ ጸለየ፣ እናም ጌታ ዝናብን ላከ። 1ኛ ነገሥት 18፡38-41

ይህን አይነት አገልግሎት እኛስ በዘመኛችን ላይ እንዴት ነው? ኃጢአትን አመቻምቸን እያየን እንዳላየን እየሆንን መሆናችን እግዚአብሔርን እንደማያስደስተው እንረዳለን?

7.  መንግስታትን ፈርተው አልኖሩም

በተለይ በዕብራውያን አስራ አንድ ላይ ያለውን የእምነት አባቶችን ታሪክ ወይም መልዕክት በትክክል ለተረዳና ላወቀው፣ ፍርሃት የሚባልን ነገር በሕይወታቸው ላይ አንመለከትም፡፡ ይልቁኑ ሲመሰክርላቸው መንግስታትን ድል ነስተው መኖራቸውን እናያለን፡፡ የእግዚአብሔርንም ስም አስከብረው ማለፋቸውን፣ በዘመናቸውም ላይ በፅድቅ ኖረው ተፅዕኖን ፈጥረው አልፈዋል፡፡

7.1.   ዳዊት- ጎልያድን

ዳዊት በታመነበት እግዚአብሔር ጎልያድን ዋነኛ የፍልስጥኤምን ተዋጊ አዋጊን ገጥሞ እስራኤልን ነፃ አውጥቷል፡፡

7.2.   ሙሴ- ፈርኦንን

ሙሴ በእግዚአብሔር ምሪትና ትዕዛዝ ፈርዖን ፊት በመቅረብ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ነፃ አውጠቷል፡፡

7.3.   ኢዩ- ኤልዛቤልን

ችላ ልትባል የማትገባዋን፣ የእግዝአብሔርን ነቢያት የፈጀችን በምንም መልኩ ኢዩ ሊታገሳት ያልቻለ ቆራጥ አገልጋይ፡፡ ውሾች እንዲበሉአት የተመኘ ጀግና አገልጋይ፣ የዘመኑ ተጽዕኖ ፈጣሪ አገልጋይ፣ ለእግዚአብሔር የጨከነ፣ ተፅዕኖን በማድረግ የእግዚአብሔርን ስም አስከብሯል፡፡

አሜን እኛም እንዲሁ ማድረግ ይሁንልን፡፡

ተባረኩ

ወንድም በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

 

የወንጌል እና የትውልድ ባለ አደራነት

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

እግዚአብሔር በዘመናት ሁሉ የልቡ የጥልቅ ሃሳብ የፈጠረው  የሰው ልጅ ደህንነት ነው። ሰው በተለይ ለነፍሱ ደህንነት፣ መኖር ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን እግዚአብሔር አሳልፎ ሰጥቶአል፣ ወደ ምድርም ክብሩን ትቶ የአባቱን ትዕዛዝ ሊፈፅም መጥቶአል። እግዚአብሔር የፈጠረው የሰው ልጅ እንዲጠፋበት አይፈልግም፣ ይልቁንም የሰውን ልጅ በአድራሻው ያለበት ድረስ መጥቶ በስም ጠርቶ ይፈልገዋል። "አዳም ሆይ ወዴት ነህ" ብሎ መምጣቱ እግዚአብሔር ምን ያህል የፍቅር አምላክ መሆኑን አስረጂ ነው። በተለይ በዚህ አለም፣ በምድር ላይ ያለን አገልጋዮች ለምንመራቸው የእግዚአብሔር ህዝቦች የዚህን ያህል ልብ ከሌለን የወንጌልን እና የትውልድን አደራ እየተወጣን አለመሆኑ ልብ ልንለው የሚገባ አቢይ ጉዳይ ነው። 

በተለይ ከቀደሙት አባቶች በውል ልንማረውና፣ ልንረዳው ይልቁኑ በህይወታችን እና በቤተክርስቲያን ልንተገብረው የሚገባ ጉዳይ ቢሆን እና ቢኖር ለወንጌልና ለትውልድ ያላቸው የፀና አቋም ነው። ከራሳቸው በላይ ለወንጌል እና ለትውልድ ያላቸው የማይናጋ እና የማይናወጥ ሙሉ ሃሳባቸው እና ማንነታቸው፣ ከራሳቸው ጥቅም በላይ ለእግዚአብሔር ህዝብ ያላቸው የፀና እምነት በተለይ ከራስ ምቾት ርቆ ከእግዚአብሔር ህዝብ ጋር መከራ ለመቀበል መወሰኑ የሙሴ ትልቅ አብነትና ምሳሌያችን ነው። 

"ለወንጌል ሁሉን አደርጋለሁ" ማለት በህይወት ላይ ይህን የመሰለ ውሳኔ የለም፣ "የማይጠፋን አክሊልን" ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያሸልም የቆራጥ አገልጋይ አቋም ነው። 

የቀደሙ አባቶች ከእግዚአብሔር የተቀበሉት አደራ በተለይ ለእግዚአብሔር ህግ እና ለትውልድ ያላቸው አደራ በጣም የሚገርም እና ለእግዚአብሔር ጉዳይ ያላቸው የፀና አቋም ዛሬ ላይ ላለን የእግዚአብሔርን መንግስት እያገለገልን ላለን ትልቅ ትምህርትና የራሳችንንም አቋም ልናይበትና ልንፈትሽበት፣ ማስተካከል የሚገባን ነገር ቢኖር እንኳን ትልቅ ትምህርት ሰጥቶን ያልፋል።

የቀደሙት የእምነት አባቶች በእግዚአብሔር፣  በእግዚአብሔር ህዝብና በእግዚአብሔር ህግ (ወንጌል) ላይ ያላቸውን አገልግሎት ስንመለከት፣ ዛሬ በድኀሰረ ስልጣኔ ዘመን ላለን ዘመነኞች አንድ አብይና አንኳር ነገር ጥሎልን ስለሚያልፍ ለትምህርት መመልከቱ ተገቢ ነው።

ባለ አደራነት ምን ማለት ነው?

ባለ አደራነት ማለት ለአንድ የተወሰነ ጉዳይ፣ ክንውን ወይም ግዴታ ለአንድ ግለሰብ ኃላፊነት ወይም ስልጣን መስጠት ማለት ነው። አንድ ግለሰብ አንድን ነገር ለሌላ ሰው ሲሰጥ፣ የተሰጠውን ኃላፊነት በብቃት በታማኝነት እና በኃላፊነት እንዲወጣ በእሱ ላይ እምነት በመጣል እና በመስጠት ጉዳዩን መጣል ነው። 

አደራ መስጠት በበላይነት፣ የውሳኔ ሰጪነት ስልጣን መስጠትን፣ ምስጢራዊ መረጃን መጋራትን ወይም ጠቃሚ ጉዳዮችን መጠበቅና ማቆየትን ሊያካትት ይችላል። 

የአደራ አብይ ጉዳይ በአደራ፣ በመተማመን የተሰጠው ሰው ማንነት ላይ በመተማመን እና በማመን ላይ የተመሠረተ ነው።

ብሉይ ኪዳን

ሙሴ ለኢያሱና ለካሌብ የሰጠው ትዕዛዝ 

እግዚአብሔር አስቀድሞ ሙሴን በኮሬብ ተራራ ተገልጦለት የነገረው ትዕዛዝ በተለይ ሕዝቡ እንዴት እና በምን አይነት መንገድ መሄድ እንዳለባቸው ለሙሴ በግልፅ ሲነግረው በዘዳግም 29:9 በውል እንመለከታለን። ለሕዝቡ ይከናወንላቸው ዘንድ መከናወኛውን እርሱም የቃል ኪዳኑ ቃሎች ይጠበቁ ዘንድ እና ያደረጉም ዘንድ ነገረው። ይህንኑ ትዕዛዝ በኢያሱ 1:7-8 ያለውን ቃል እግዚአብሔር መልሶ ኢያሱን ሙሴ ያዘዘህን በማለት የአደራን መቀበል ያስታውሰዋል። ይህንኑ ቃል በአደራነት ኢያሱም ለእስራኤል ቤት ሲናገር እንመለከታለን።

ኢያሱ የእስራኤል ሽማግሌዎችን

በተለይ ኢያሱ ከሙሴ መሞት በኋላ የእስራኤልን ህዝብ ሊመራ ከሙሴ በአደራ የተቀበለ ተተኪ አገልጋይ ነው። ካሌብም አብሮት የተቀበለ መሆኑ አይዘነጋም። የመከናወንና የስኬት መንገዱ ያለው በእግዚአብሔር ህግ ውስጥ እንደሆነ ሙሴ አበክሮ የነገረው ሲሆን ይህንንም እንዲያስቀጥል እግዚአብሔር ሙሴ የነገረውን ኢያሱን አስታወሰው። ኢያሱ 1:7-8 መመልከት ይቻላል።

ኢያሱም እንዲሁ በሽምግልናው በተለይ በመሞቻው ጊዜ የእስራኤልን ሽማግሌዎች እና ነገዶች በመሰብሰብ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ከእግዚአብሔር እና ሲመራቸው ከነበረው ሙሴ በአደራ የተቀበላቸውን ህዝቦች ስኬት እና መከናወን እንዲሆንላቸው ከእግዚአብሔር ህግ ፈቀቅ እንዳይሉ የእግዚአብሔርን ህግ በአደራ እንደ ተቀበለ በአደራ ሲሰጣቸው በኢያሱ 23:1-6 መመልከት እንችላለን። 

ዳዊት ልጁን ሰለሞንን

ዳዊት ከልጅነት እግዚአብሔር በብዙ የህይወት ጉዳና ውስጥ ያሳለፈው፣ እግዚአብሔር በምድረበዳ በእረኝነት ህይወቱ ብዙ ፈተናዎችን በእግዚአብሔር ሃይልና እርዳታ የኖረ፣ የመሪነትን እና የጦረኝነትን ህይወት፣ የእረኝነትን ህይወት እግዚአብሔር ያሰለጠነው ትልቅ የእግዚአብሔር ልብ ያለው ጀግና ንጉስ ነው። በተለይ በመዝሙር 119 ላይ የፃፋቸው በእግዚአብሔር ህግ ላይ በዚህ በተጠቀሰው መዝሙሩ ላይ እውቀቱን መረዳት እንችላለን። ምን ያህል ሕጉን ይዘን ስንኖር መከናወን እንዳለ ቁልጭ አድር ጎ ያሳየናል። ለዚህ ነው በተለይ የዳዊት የህይወቱ ማብቂያ ላይ ከመሞቱ አስቀድሞ ምን ማድረግ እንዳለበት በእግሩ በተተካው ልጁን ሰለሞንን በብርቱ ሲመክረው የምናየው። 1ኛ ነገሥት 2:3 ላይ ሰለሞን ምን ማድረግ እንደሚገባው የህይወት ዘመን ምክርን ዳዊት አባቱ በአደራ ሲመክረውና አስረግጦ ሲነግረው በዚህ ምዕራፍ ላይ እንመለከታለን። 

በዚህ ትምህርት ምን ያህል ዳዊት ለእግዚአብሔር ህግ እና ለትውልድ አደራነት እንደሚጨነቅ መመልከት እንችላለን። አደራነት ለቀጣይ ለእግዚአብሔር ህግና ለትውልድ ማሰብ መቻል ማለት ነው።

አዲስ ኪዳን

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለጴጥሮስ የሰጠው አደራ

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አባቱ ከመሄዱ አስቀድሞ ለጴጥሮስ የነገረው የአደራ መልዕክት እንደነበረ ሁላችን የማንዘነጋው ብርቱ ጉዳይ ነው። ይህንንም አደራ እንደምስክር የተመለከተው ዮሐንስ በመልዕክቱ በጥንቃቄ ሰድሮ ዛሬ ላይ ላለን አገልጋዮች ፅፎልናል።

 አደራ አደራን በሰጠው በሰጪው ልክ ተረድተን እና ተገንዝበን የምንቀበለው ብርቱ መልዕክት እና ትዕዛዝ ነው። በተለይ በዮሐንስ 21:15-17 ያለው መልእክት ለእኛም በዚህ ዘመን ላለነው አገልጋዮች አደራ ምን ያህል ከባድ የሆነ ኃላፊነትና ተጠያቂነት ያለው አገልግሎት መሆኑን መረዳትና ማወቅ እንዳለብን በአፅንኦት ያሳየናል።

ጌታ ኢዩበዘኑ ሁሉ ምን ያህል ለትውልድ እንደሚጨነቅ ማየት የምንችለው ብርቱ እና ወሳኝ ጉዳይ ነው። ምክንያቱም ለቀጣይነቱ በትውልድ ላይ ምን ያህል መሠራት እንዳለበት አስረግጦ ይነግረናል። "ህፃናት ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ አትከልክሉአቸው" ማለቱ ለትውልድ ምን ያህል አፅንኦት ሰጥቶ እንደሚናገር ማወቅ ይቻላል።

ሐዋርያው ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ 

ጢሞቴዎስ ልጄ ሆይ፥ አስቀድሞ ስለ አንተ እንደ ተነገረው ትንቢት፥ በእርሱ መልካም ጦርነት ትዋጋ ዘንድ ይህችን ትእዛዝ አደራ እሰጥሃለሁ፤ 1ኛ ጢሞቴዎስ 1፥18።

በመጨረሻም፦

ነገር ግን ወንጌልን አደራ ይሰጠን ዘንድ እግዚአብሔር የታመንን ሆነን እንዳገኘን መጠን፥ እንዲሁ እንናገራለን፥ ልባችንን የሚመረምር እግዚአብሔርን እንጂ ሰውን ደስ እንደምናሰኝ አይደለም። 1ኛ ተሰሎንቄ 2፥4።

ጸሎት

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

በምድር ላይ ካሉ ሐይማኖታዊ ነክ ከሆኑ እምነቶች አንዱ ክርስትና ነው። ክርስትና በባህሪው ዋነኛ አድርጎ ከሚንቀሳቀስባቸው አብይ ሚስጥራት መካከል አንዱ ጸሎት ነው። ጸሎት ለክርስቲያኖች የሁልጊዜ የማይቋረጥ ተግባራቸውና ስራቸው ነው። ሳይከውኑት የሚውሉት ወይም የሚያድሩት ጉዳይ አይደለም።

ጸሎት በሚጸልየውና ጸሎትን በሚሰማው በእግዚአብሔር መካከል ያለን ቁርኝት ማሳያ እና ማመልከቻ ነው።

ጸሎት በውስጡ የሚያካትታቸው አቢይ ጉዳዮች፥ ምስጋና፣ ልመና፣ ምልጃ እና በአጠቃላይ እነዚህን አካትቶ አምልኮ ነው። 

ጸሎት የሰው ልጅ የማይችለውን ጉዳይ እግዚአብሔር አንተ ትችላለህ ብሎን ልመናን ማቅረቢያ መንገድ ነው። ያለ ጸሎት ክርስትና አይታሰብም፣ ሊነጣጠልም የሚችል ጉዳይ አይደለም። 

ጸሎት ከሚደረግባቸው አይነቶች መካከል፦

1- በግል ሊቀርብ የሚችል፦ በተናጠል

2- በቡድን የሚቀርብ፦ በማህበር

3- በባለትዳሮች የሚቀርብ፦ የራሳቸውን ጊዜና ቦታ በመውሰድ

4- እንደ ሃገር የሚቀርብ፦ ለድንገተኛ ጥሪ ሲሆን (እግዚዮታ)

5- በቤተክርስቲያን፦ ለአማኞች የአንድነት ጊዜ ሲኖር የሚደረጉ የጸሎት አይነቶች ናቸው።

በተለይ ክርስቲያን የጸሎት ምንነትን እና እንዴትነት የጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ልንማር የግድ ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአርባ ቀናት ያህል ባለማቋረጥ ጸልዮአል። ለጸሎትም ይተጋ ነበር። የሉቃስ ወንጌል 22:39-49 (መከራው፣ ጽዋው እንዲያልፍ ጸለየ)

ጸሎት የልባችንን መሻት የምንለምንበት ዋነኛ መንገድ ነው። መዝሙረ ዳዊት 37:4

ምኞታችንን ከበረከቱ እንዲያጠግበን የምንለምንበት ነው። መዝሙረ ዳዊት 103:5

1- ጸሎት ልናበዛው የሚገባን ነው፦ ምናሳንሰው አይደለም

የምንፈልገውን ከእግዚአብሔር እስከምናገኝ ድረስ የምንከውነው ሥራ ነው፣ የምንፈልገውን እስከምናገኝ  አብዝተን ልናደርገው የሚገባ ነው።

ጸሎትዋንም በእግዚአብሔር ፊት ባበዛች ጊዜ ዔሊ አፏን ይመለከት ነበር። 1ኛ ሳሙኤል 1:12

2- በልብ የምንናገረው ነው፦ ሚስጢር ነው

ድብቅ የሆነን ለእግዚአብሔር ብቻ የምንነግረው ነው። ማንም ሊሰማው የማይገባ ነገራችንን የምንገልጽበት ነው። ሐናም በልብዋ ትናገር ነበር፤ ድምፅዋም ሳይሰማ ከንፈርዋን ታንቀሳቅስ ነበር፤ ኤሊም እንደ ሰከረች ቆጠራት። 1ኛ ሳሙኤል 1:13

3- የምንጮኸው ነው፦ ጉዳያችንን አበክረንና አጽንኦት ሰጥተን የምናቀርበው ነው

ወደ እግዚአብሔር የምንጮኸው፣ እግዚአብሔርም የሚመልስበት አቀራረብ ነው። ክርስቲያን አንዳች የሚደንቅን ነገር የሚፈልግ ነው። ለዚህም ነው እግዚአብሔር እንደ ትዕዛዝ የሚነግረን። "ወደ እኔ ጩኽ፥ እኔም እመልስልሃለሁ፤ አንተም የማታውቀውን ታላቅና ሃይለኛ ነገርን አሳይሃለሁ። ትንቢተ ኤርምያስ 33:3

4- ጸሎት በትጋት ይደረጋል

ጸሎት አንዴ ሲመቸን፣ አንዴ ሳይመቸን የምናደርገው አይደለም። በምቾትም ይሁን በማይመች ሁኔታና ጊዜ የምናደርገው አይደለም። የእኛን ያለመድከም ይፈልጋል።

ጸሎት በብርታት ጊዜ የምንተወው፣ በድካም ጊዜ የምንቀጥለው አይደለም። ከሁኔታ ያለፈ ነው። በሁኔታም የሚወሰን፣ ወይም የሁኔታ ጥገኛ አይደለም። በምንም ሁኔታ እንሁን የምንተወው አይደለም። ስለዚህ፦ "ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ፤ መንፈስስ ተዘጋጅታለች ሥጋ ግን ደካማ ነው አለው። ማቴዎስ 26:41።

ወደ ደቀመዛሙርት መጣ፤ ተኝተውም አገኛቸውና ጴጥሮስን፦ እንዲሁም ከእኔ ጋር አንዲት ሰዓት እንኳ ልትተጉ አልቻላችሁምን? ማቴዎስ 26:40

5- ጸሎት ያለማቋረጥ የሚደረግ ነው

አንድ ወቅት ጸልየን በሌላ ቀን የምንተወው አይደለም፣ ጸሎት የሁልጊዜ ሥራችን ነው፣ ከእግዚአብሔር ጋር የምንነጋገርበት ነው። ስለዚህ ልናቋርጠው የሚገባን አይደለም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር በኖረበት ጊዜ ከከወናቸው ድርጊቶች አንዱ ባለማቋረጥ መጸለዩ ነው። ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚለን፦ ሳታቋቂጸልዩ፤ በሁሉ አመስግኑ፤ ይህ የእግዚአብሔር ፈቃድ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ እናንተ ነውና። 1ኛ ተሰሎንቄ 5:17-18።

የቀደሙ አባቶችና ጸሎት

የቀደሙ አባቶች ከጸሎት ጋር የጠነከረ ቁርኝት አላቸው። ጸሎት እጅግ በእነርሱ ህይወት ውስጥ የተጣበቀ ነው። በጸሎት አይደራደሩም፣ ወደ ኋላም አይሉም፣ ጸሎት ልማዳቸው ነው። በምንም አይነት ሁኔታ ውስጥ ይገኙ ጸሎትን አያቋርጡም።

1- አብርሃም፦ የእምነት አባት

በአብርሃም ሚስት በሣራ ምክንያት በአቢሜሌክ ቤት ማህፀኖችን ሁሉ ዘግቶ ነበርና አብርሃም ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ሁሉም ተፈወሱ ወለዱም።  ዘፍጥረት 20:17-18

2-ይስሐቅ፦ ለአባቱ አብርሃም የታዘዘ

ስለ ሚስቱ መካንነት ጸለየ፣ እርሷም ፀነሰች። መካንነቷ ቀረ፣ ተወገደ፣ ዘር ተተካ። ዘፍጥረት 25:21

3- ሙሴ፦ ቁጣ እንዲመለስ ጸለየ

እግዚአብሔር በሕዝቡ ኃጢአት ምክንያት በመቆጣቱ፣ ቁጣው በመንደዱ ምክንያት እግዚአብሔር ከቁጣው  እንዲመለስ እግዚአብሔርን ይለምን ይጸልይ ነበር። ዘጸአት 8:30፤ ዘኁልቁ 11:2፤ 21:8።

4- ሃና፦ የስለት ጸሎት

ሃና በማህፀኗ መዘጋት፣ በመሃንነት የተነሳ በጣውንቷ ማስቆጣት ተበሳጭታ ወደ እግዚአብሔር የስለት አዘል ጸሎት ጸለየች፣ እግዚአብሔርም ሰማት፣ ልጅም አገኘች በስለቷም መሠረት ለእግዚአብሔር መልሳ ሰጠች። ስለት አዘል ጸሎት አቀረበች። 1ኛ ሳሙኤል 1:10፤ 1:12-14።

5- ኤልሳዕ- ሙት ህፃን በእጁ ተፈወሰ

ኤልሳዕ ሁሉን ወደሚችል ወደ እግዚአብሔር ጸለየ የሞተውም ህፃን በእጁ እግዚአብሔር አስነሳው። 2ኛ ነገሥት 4:30-34፤ 6:18።

ስለዚህ ጸሎት ከእኛ ከክርስቲያኖች ተነጥሎ፣ ተለይቶ የሚታይና የሚገኝ አይደለም። ጸሎት ለክርስቲያኖች ወሳኝ ጉዳይ ነው።

ስለዚህ የጸሎት ጊዜና ቦታ በተለይም የጸሎት መሰዊያ ሊኖረን ይገባል። የጸሎት ጊዜና ቦታ ይኑረን፣ የጸሎት መሠዊያን እናበጅለት። 

የቀደሙት የእምነት አባቶች ከሚለዩባቸው ባህሪያት አንደኛው መለያ ባህሪያቸው በጸሎት ማመንና የጸሎት ስፍራ ማበጀትና ማዘጋጀታቸው ነው።

ከፊታችን ትልልቅ ፈተናዎች ይመጣሉ ይህንንም የምናልፈው በጸሎት ብቻ ነው። እግዚአብሔርን በማነጋገር። 

ጸሎት በእግዚአብሔር ፊት ሆነን እጅግ ትንሽ ጊዜን በመውሰድ የምንለምንበት፣ እጅግ ብዙ ከእግዚአብሔር የምንሰማበት ነው።

በመጨረሻም፦ "... የጻድቅ ሰው ጸሎት በሥራዋ እጅግ ኃይል ታደርጋለች።" ያዕቆብ 5:16

ስለዚህ ቅዱስ ሁሉ በምቹ ጊዜ ወደ አንተ ይለምናል፤ ብዙ የጥፋት ውኃም ወደ እርሱ አይቀርብም። መዝሙር 32:6።

አቤቱ፥ በመልካሙ ጊዜ ጸሎቴ ወደ አንተ ነው፤ አቤቱ በምህረትህ ብዛት በማዳንህም እውነት አድምጠኝ። መዝሙር 69:13

ለምኑ፥ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፥ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፥ ይከፈትላችሁማል። ማቴዎስ 7:7።

ተባረኩ

አገልጋይ በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

ፍጹምነትን መያዝ (INTEGRITY, JUSTIFICATION, PERFECTION)

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

ክርስትና በእግዚአብሔር ፊት በምመካድ፦ለሰው ህይወትና መስተጋብር የምንገልጸው ሕይወት ነው። እግዚአብሔር የሚጠላውን ጠልተን፣ እግዚአብሔር የሚወደውን ወድደን እግዚአብሔርን እያስደሰትን የምንኖረው ሕይወትና ተግባራዊ እንቅስቃሴ ነው። 

Read more: ፍጹምነትን መያዝ (INTEGRITY,...

Subcategories

ነገረ ድነት/ Salvation

  • የታጠቀ ትውልድ
  • የትውልድ አደራ
  • እስክንድሮሶች
  • ዲዮጥራጢስ
  • መሰረተ እምነት (2)

Article Categories

  • Literature/ስነ-ጽሑፍ
  • Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ
  • The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ
  • Testimony/ምስክርነት
  • Religious News/ሐይማኖታዊ ዜና
  • Churches/ቤተ ክርስቲያን

Login Form

  • Forgot your password?
  • Forgot your username?
Copyright © 2026 yegizewkal. All Rights Reserved.