yegizewkal
ቃልህ ተገኝቶአል እኔም በልቼዋለሁ አቤቱ፥ የሠራዊት አምላክ ሆይ፥ በስምህ ተጠርቻለሁና ቃልህ ሐሤትና የልብ ደስታ ሆነኝ። ትንቢተ ኤርምያስ 15፥16

  • Home/መነሻ ገጽ
  • Gospel Thoughts/የወንጌል አስተምህሮ
    • ነገረ ድነት/Salvation
  • The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ
    • Literature/ስነ-ጽሑፍ
    • ከመጽሐፍት ዓለም
  • Churches/ቤተ ክርስቲያን
    • Religious News/ሐይማኖታዊ ዜና
  • Testimony/ምስክርነት
  • ማስታወቂያ/Advertisement
  1. You are here:  
  2. Home
  3. Gospel Thoughts/የወንጌል አስተምህሮ

Gospel Thoughts/የወንጌል አስተምህሮ

የተቃኘንበትን ቅኝት ያጠፉ ቅኝቶች

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

 

የተቃኘንበትን ቅኝት ያጠፉ ቅኝቶች

 

 

ቀድሞ የመጣንባቸው ትምህርቶች በክርስቶስ ትምህርት የተቃኘንበት፣ ያስተማሩንም የተቃኙበት ቅኝት የክርስቶስ ትምህርት ላይ ሆኖ ዛሬ ላይ መቃኘታችንም ይሁን ቅኝታችን በክርስቶስ ላይ ሳይሆን "ሃሳባቸው ምድራዊ በሆኑ" ከክርስቶስ ትምህርት ቅኝት ውጪ በሆኑ ከምድር የሚሰፉና የሚያጣብቁ ቅኝቶች መብዛታቸው የመከራ ጊዜ ሲመጣ መቋቋም የማይችሉትን ማፍራታቸው ቅኝታቸው ላይ ፈርጀ ብዙ ችግር መኖሩን ያሳብቃሉ።

የዘመኑ የትምህርት ቅኝቶች ለጊዜውም ቢሆን ደስታን ቢያጭርም ለመጻኢው ጊዜ ዘላቂና ቋሚ ያለመሆኑ ቅኝቱ ቢያስደስትም ከማስጨፈር ያለፈ ዘላቂውንና ዘላለማዊ አጀንዳን ከማናጋት ያለፈ እያስረሳን መሆኑን ለአፍታም ሰከን ብለን ነገሮችን አለመቃኘትና መንገድን አለመሰለል ትልቁ ውድቀታችን እንደሆነ አለማወቅ ሐሳባችን በዘመኑ ቅኝትና አጀብ ተዘናግተን ከግንዱ በመለየታችን በፍሬም አለመገለጣችን እንዲያው ባለማፍራታች ተቆርጠን ወደሚነደው ሳንጣል ከወዲሁ መንቃት ተገቢ ነው።

ከቅኝቶቹ በጥቂቱ

ባልገመትናቸው እና ቀድሞ በክርስቶስ እና በክርስቶስ ላይ በነበራቸው ትምህርት እና አቋማቸው የምናውቃቸው ዛሬ ላይ በቀደመው በተነሱበት እና በጀመሩት ቅኝት አለመሔዳቸው ዛሬ ላይ ግን ቃናቸው ጠፍቶ ነገራቸው የኮመጠጠ ለአፍም የጎመዘዘ ነገራቸው ዛሬ ላይ ክርስቶስን ብሎ ለሚኖርና ክርስቶስን ብቻ ለመስበክ የተነሳን አመቺ እና አማራጭ ባሉት መንገድና ብሒል የነዚህን ቅኝት ሊያጠፉ መነሳታቸው የራስን ቅኝት አቀንቅኑልን በሚሉ ለመዋጥ የተነሱ የዘመኑ ተኩላና ቀበሮ አምራቾች ቅኝት የጠፋባቸው፣ ቃና ለዋጮችን ወግድ ብሎ መሸሹ ያለ አማካሪ የሚወሰን ቁርጠኝነት ነው።

እየጠጣን የነበርነውን ንፁሁን ውሃችንን ዛሬ ላይ በተነሱ አገልጋዮች (መነሻቸውን በደረሱበት እንለካ) ነብዩ ሕዝቅኤል እንዳለው በእግሮቻቸው አደፈረሱት፣ መንጋውም ይህንኑ እየጠጣ ጤናማ የነበረውን የመንፈሳዊ ጤንነቱ ታመመ። እንደ ጳውሎስ ጤናማ ቃል የሚናገር ጠፋ። ጤናማ ንግግርም ጠፋ። “በጎቼም በእግራችሁ በረገጣችሁት ይሰማራሉ በእግራችሁም ያደፈረሳችሁትን ይጠጣሉ።” — ሕዝቅኤል 34፥19።

መልዕክት አልባ ቆንጆ ዜማ

ብዙ ነገሮቻችን በላይ ከላይ ዕይታ ያማሩ ማር ቅብ የሆኑ ነገር ግን መልእክት የለሽ፣ ውሃ የማያነሱ፣ ሰማይ የማያውቀው እውቅና አልባ ነገሮቻችን ዛሬ ላሉት ትውልዶች አድንቆ ከመሄድ ውጭ ህይወት ላይ ጠብ የማይል፣ ከእግዚአብሔር የማያገናኝ እያጫወተ ዋናውን የሚያዘናጋ የጣፋጭ ቅኝቶች፣ የዘላቂ ዋስትና የማይሆኑ ብዙ ነገሮቻችን መዳሰስ፣ መታየት፣ መገምገም፣ ማስወገድ ተገቢ ነው።

በተለይ ዘመናችን ላይ እየተለቀቁ ያሉ አስተምሮቶች ከወንጌል እውነታ ውጪ የሆኑ አውድ አፈንጋጭ አስተሳሰቦች ቦታውን በመያዝ እውነትን ሰዎች እንዳይረዱ አዚም ያደረጉ፣ ክርስቶስ እንደተሰቀለ፣ እንደ ሞተ፣ ሞቶም እንደተነሳ፣ ኋላም እንደሚመጣ የማስተምሩ እንግዳ ትምህርቶች የእግዚአብሔርን ቤት እየሞሉት እንዳሉ ይታያል። በተለይ በነገረ ድነት ላይ ያለን አመለካከት መጽሐፍ ቅዱሳዊ እንድምታን አለመያዙ ግርታንና ግርግር ፈጥሮ ይታያል። “ልዩ ልዩ ዓይነት በሆነ በእንግዳ ትምህርት አትወሰዱ፤ ልባችሁ በጸጋ ቢጸና መልካም ነው እንጂ በመብል አይደለም፤ በዚህ የሚሠሩባት አልተጠቀሙምና።” — ዕብራውያን 13፥9።

ከክርስቶስ ትምህርት ነጣይ

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዋናነት ወደ ምድር መምጣቱ ለምን እንደሆነ በውል ካለመረዳት፣ ካለማወቅ የተነሳ ዛሬ በምድራችን ላይ የሚሰበኩት፣ በትምህርትም መልክ የሚሰጡት ጨርሶውኑ ክርስቶሳዊ ትምህርቶች አይደሉም። የክርስቶስ ትምህርት ዓላማን የሳተና ያፈነገጠ ነው።

ምናልባትም የክርስቶስ ትምህርት ምንድን ነው ልንል እንችላለን፣ የክርስቶስን ትምህርት ለመረዳትና ለማወቅ የተራራውን ስብከት መመልከቱ ተገቢ ሲሆን በተጨማሪም የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ህይወቱን መመልከት ከበቂ በላይ ነው። (ማቴዎስ ወንጌል 5፣6፣7) መመልከት ይቻላል። “ለሚወጣ ሁሉ በክርስቶስም ትምህርት ለማይኖር ሰው አምላክ የለውም፤ በክርስቶስ ትምህርት ለሚኖር አብና ወልድ አሉት።” — 2ኛ ዮሐንስ 1፥9።

ከክርስቶስ ነጣይ ትምህርት

 

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዋናነት ወደ ምድር መምጣቱ ለምን እንደሆነ በውል ካለመረዳት፣ ካለማወቅ የተነሳ ዛሬ በምድራችን ላይ የሚሰበኩት፣ በትምህርትም መልክ የሚሰጡት ጨርሶውኑ ክርስቶሳዊ ትምህርቶች  አይደሉም። የክርስቶስ ትምህርት ዓላማን የሳተና ያፈነገጠ ነው።

 

ምናልባትም የክርስቶስ ትምህርት ምንድን ነው ልንል እንችላለን፣ የክርስቶስን ትምህርት ለመረዳትና ለማወቅ የተራራውን ስብከት መመልከቱ ተገቢ ሲሆን በተጨማሪም የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ህይወቱን መመልከት ከበቂ በላይ ነው። (ማቴዎስ ወንጌል 5፣6፣7) መመልከት ይቻላል። “ለሚወጣ ሁሉ በክርስቶስም ትምህርት ለማይኖር ሰው አምላክ የለውም፤ በክርስቶስ ትምህርት ለሚኖር አብና ወልድ አሉት።” — 2ኛ ዮሐንስ 1፥9።

 

ሐዋርያት ተለይተው የቆሙለትን አለማወቅ

ሐዋሪያት በትምህርታቸውም፣ በሕይወታቸውም አንድም ቀን በምድራዊ ነገር ላይ ትኩረታቸውን እንዲያደርጉ እንጂ ምድር ነክ አሊያም ምድራዊ የሆነን ነገር በሚያስተምሩአቸው ዘንድ ነግረውም አስተምረውም አያውቁም። አጽንኦት ሰጥተው የሚያስተምሩትና የሚነግሩት ትልቁ ሥራቸው ኢየሱስን አሳይተው ከማለፍ ውጪ ሌላ አጀንዳ፣ መልእክት፣ ስብከት የላቸውም። ነቢያትም ቢሆኑ በሩቅ ይሁን በቅርብ ኢየሱስን አሳይተው፣ ነግረው፣ ተናግረው ነው ያለፉት። ሕዝብን ከምድር አላገናኙም፣ ባለፈና በሚያልፍ ነገር ላይ ሕዝብን አላስተማሩም፣ ኢየሱስን ግን በጊዜውም አለጊዜውም ተናግረው፣ ዘላለማዊውን ጉዳይ ብቻ፣ የሰማዩን ብቻ ተናግረው፣ ተርከው አልፈዋል። በእርግጥም በነቢያት እና በሐዋሪያት መሠረት ላይ መታነፃቸውን በትክክል በምቾትም ይሁን በመከራ ውስጥ ሰብከው አልፈዋል። በተለይ በምቾት ውስጥ ሆነው ከሰበኩት ይልቅ በመከራ ውስጥ ሆነው የሰበኩት በእጅጉ የተለየና የሚበልጥ ነበረ። “በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፥ የማዕዘኑም ራስ ድንጋይ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፤” — ኤፌሶን 2፥20።

1- ጳውሎስና በርናባስ

ሀ- ወንጌልን

“እንዲህም አሉ፦ እናንተ ሰዎች፥ ይህን ስለ ምን ታደርጋላችሁ? እኛ ደግሞ እንደ እናንተ የምንሰማ ሰዎች ነን፥ ከዚህም ከንቱ ነገር ሰማይንና ምድርን ባሕርንም በእነርሱም ያለውን ሁሉ ወደ ፈጠረ ወደ ሕያው እግዚአብሔር ዘወር ትሉ ዘንድ ወንጌልን እንሰብካለን።” — ሐዋርያት 14፥15።

ለ- ክርስቶስን

“እኛ ግን የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን፤ ይህም ለአይሁድ ማሰናከያ ለአሕዛብም ሞኝነት ነው፥” — 1ኛ ቆሮንቶስ 1፥23።

ሐ- የምስራቹን

“እኛም ለአባቶች የተሰጠውን ተስፋ የምስራቹን ለእናንተ እንሰብካለን፤” — ሐዋርያት 13፥32።

የጳውሎስ አቋም

እርግጥ ነው ጳውሎስ የነበረበትን ሕይወትና ልምድ በሁላችን የታወቀ ነው። “እኔ ግን በሥጋ ደግሞ የምታመንበት አለኝ። ሌላ ሰው ማንም ቢሆን በሥጋ የሚታመንበት እንዳለው ቢመስለው፥ እኔ እበልጠዋለሁ።”— ፊልጵስዩስ 3፥4። “በስምንተኛው ቀን የተገረዝሁ፥ ከእስራኤል ትውልድ፥ ከብንያም ወገን፥ ከዕብራውያን ዕብራዊ ነኝ፤ ስለ ሕግ ብትጠይቁ፥ ፈሪሳዊ ነበርሁ፤” — ፊልጵስዩስ 3፥5። “ስለ ቅንዓት ብትጠይቁ፥ ቤተ ክርስቲያንን አሳዳጅ ነበርሁ፤ በሕግ ስለሚገኝ ጽድቅ ብትጠይቁ፥ ያለ ነቀፋ ነበርሁ።” — ፊልጵስዩስ 3፥6። “ነገር ግን ለእኔ ረብ የነበረውን ሁሉ ስለ ክርስቶስ እንደ ጉዳት ቈጥሬዋለሁ።”— ፊልጵስዩስ 3፥7። “አዎን፥ በእውነት ከሁሉ ይልቅ ስለሚበልጥ ስለ ክርስቶስ ኢየሱስ ስለ ጌታዬ እውቀት ነገር ሁሉ ጉዳት እንዲሆን እቈጥራለሁ፤ ስለ እርሱ ሁሉን ተጐዳሁ፥ ክርስቶስንም አገኝ ዘንድ፥ በክርስቶስም በማመን ያለው ጽድቅ ማለት በእምነት ከእግዚአብሔር ዘንድ ያለው ጽድቅ እንጂ ከሕግ ለእኔ ያለው ጽድቅ ሳይሆንልኝ፥ በእርሱ እገኝ ዘንድ ሁሉን እንደ ጕድፍ እቈጥራለሁ፤” — ፊልጵስዩስ 3፥8-9።

ብልጽግና

ብዙውን ጊዜ የክርስትናን ሕይወት በምድራዊ ሐብትና ቁስ ስንለካው፣ ስንገምተውና፣ ስንተምነው እንገኛለን፣ በዚህም ጉዳይ አስተምህሮ አዘጋጅተን እንሰብካለን። እግዚአብሔር የእጆቻችንን ሥራ በእርግጥም ይባርካል ሆኖም ግን የመንፈሳዊነት በረከት መለኪያ ግን አይደለም፣ ጨርሶውንም ሊሆን አይችልም። መቁጠር ካለብን ካለብን ምንቆጥረው ይሄን የእግዚአብሔር ቃል ይዘን ብቻ ነው። ያላቸውን ትተው የተከተሉ እንዳሉ መዘንጋት የለብንም። "ሁሉን ትተን ተከተልንህ"፣ ሙሴ ከፈርኦን ቤት ትቶ መውጣቱን መዘንጋትም የለብንም፣ ጳውሎስ ሁሉን እንደ ጉድፍ ቆጥሮ ለወንጌል መኖሩን አንዘንጋ። “በክርስቶስ በሰማያዊ ስፍራ በመንፈሳዊ በረከት ሁሉ የባረከን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት ይባረክ።” — ኤፌሶን 1፥3።

ጥንቃቄ 

በሚከተሉት አብይ ጉዳዮች አስተውሎት ይኑረን

1- መጽሐፍ ቅዱስ ከሚለኝ ውጪ አይደለሁም

ስሁት ከሆኑ አስተምህሮዎች መካከል በተለይ "መንፈስ ነኝ/ነን) በሚል አስተምህሮዎቻቸው የምናውቃቸው ብዙዎች የመኖራቸውን ያህል ትንንሽ አምላኮች ነን የሚሉት ብቅ ማለታቸው ምን ያህል መንፈሳዊ ዝቅጠት ውስጥ መገኘታችንን ያሳየናል። መጽሐፍ ቅዱሳችን አፅንኦት ያልሰጠበትን ለመናገር አለመቸኮል መልካም ነው። ትኩረት በተሰጠው ላይ መገኘት ተገቢ ነው። “ስለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ ልጅ ነህ እንጂ ባሪያ አይደለህም፤ ልጅም ከሆንህ ደግሞ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሽ ነህ።” — ገላትያ 4፥7። “ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም፤ ባርያ ጌታው የሚያደርገውን አያውቅምና፤ ወዳጆች ግን ብያችኋለሁ፥ ከአባቴ የሰማሁትን ሁሉ ለእናንተ አስታውቄአችኋለሁና።” — ዮሐንስ 15፥15።

2- መጽሐፍ ቅዱስ የነገረኝን እንጂ ሰው የነገረኝን አላምንም

በተለይ ጥቅም ተኮር፣ ንዋይን መሠረት ያደረገ፣ ቁሳዊ ከሆኑ፣ ክርስቶስን ከማያሳዩን እጅግ በጣም ፈቀቅ ልንላቸው ይገባል። ራስ ተኮር ከሆኑ፣ ክርስቶስ ተኮር ካልሆኑት መሸሹ ተገቢ ነው ። ምክንያቱም ዘላለማችንን ከሚነኩና ሊያሳጡ ከሚያደርጉ ነገሮች ሁሉ መሸሹ በጣም ያዋጣል። “ነገር ግን እኛ ብንሆን ወይም ከሰማይ መልአክ፥ ከሰበክንላችሁ ወንጌል የሚለይ ወንጌልን ቢሰብክላችሁ፥ የተረገመ ይሁን።” — ገላትያ 1፥8። “አስቀድመን እንዳልን እንዲሁ አሁን ሁለተኛ እላለሁ፥ ከተቀበላችሁት የተለየውን ማንም ቢሰብክላችሁ የተረገመ ይሁን።” — ገላትያ 1፥9።

3- መጽሐፍ ቅዱስን መርህ ያላደረገ ትምህርት አልቀበልም

ዛሬ ዘመን ሰው በተለይ ክርስቲያን በምድራዊ ነገር እጅግ መባረክን ይሻል። መመኘቱ መልካም ነው፣ አይከፋም። ባራኪውንና መባረኪያውን ግን ወደ ጎን ማድረጉ ግን ተገቢ አይደለም። ይህ ነገር እይታችንን ከዘላለማዊ አጀንዳችን ላይ ያነሳል፣ ሸውራራ ከሚያደርጉ ነገሮች አንዱ ነው። በተለይ ብድራታችንን ትኩር ብለን እንዳናይ፣ የክርስትና ጉዞአችንም ላይ እንቅፋት እና ሳንካን ይፈጥርብናል። “አምላካችሁንም እግዚአብሔርን ታመልኩታላችሁ፥ እርሱም እህልህንና ውኃህን ይባርካል፤ በሽታንም ከመካከልህ አርቃለሁ።” — ዘጸአት 23፥25።

4- በመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ትምህርት ላይ የማያተኩረውን አስተምህሮ አልቀበልም

ክርስቶስ ትልቁ አላማው ከእግዚአብሔር ጋር የለንን የተቋረጠውን ህብረትና አንድነት ማስኬድና ህይወት ሊሆንልንና ሊበዛልን፣ በዘላለም ከጀንዳ ላይ ተካትተን፣ በሰማያዊ ስፍራ በመንፈሳዊ በረከት መባረካችንን ለማሳየትና እንድንይዘው፣ ይህም ትልቁ በረከታችን አንድ ብለንም የምንቆጥረው ነው። “ለሚወጣ ሁሉ በክርስቶስም ትምህርት ለማይኖር ሰው አምላክ የለውም፤ በክርስቶስ ትምህርት ለሚኖር አብና ወልድ አሉት።” — 2ኛ ዮሐንስ 1፥9። “ማንም ወደ እናንተ ቢመጣ ይህንም ትምህርት ባያመጣ በቤታችሁ አትቀበሉት ሰላምም አትበሉት፤”— 2ኛ ዮሐንስ 1፥10።

                        በመጨረሻም

ሀ- ከአለማዊነት መራቅ

“ጢሞቴዎስ ሆይ፥ በውሸት እውቀት ከተባለ ለዓለም ከሚመች ከከንቱ መለፍለፍና መከራከር እየራቅህ፥ የተሰጠህን አደራ ጠብቅ፤” — 1ኛ ጢሞቴዎስ 6፥20።

ለ- ለመንፈሳዊ ጤንነት ጤናማ ቃል መያዝ

“በክርስቶስ ኢየሱስ ባለ እምነትና ፍቅር አድርገህ፥ ከእኔ የሰማኸውን ጤናማ ቃል ምሳሌ ያዝ፤” — 2ኛ ጢሞቴዎስ 1፥13።

ሐ- አደራን መጠበቅ

“መልካሙን አደራ በእኛ በሚኖረው በመንፈስ ቅዱስ ጠብቅ።” — 2ኛ ጢሞቴዎስ 1፥14።

መ- በተማሩት መኖር

“አንተ ግን በተማርህበትና በተረዳህበት ነገር ጸንተህ ኑር፥ ከማን እንደ ተማርኸው ታውቃለህና፤” — 2ኛ ጢሞቴዎስ 3፥14።

ሠ- ቅዱሳን መጻሕፍትን ማወቅ

“ከሕፃንነትህም ጀምረህ ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን፥ መዳን የሚገኝበትን ጥበብ ሊሰጡህ የሚችሉትን ቅዱሳን መጻሕፍትን አውቀሃል።” — 2ኛ ጢሞቴዎስ 3፥15።

ቸር ይሁን

ወንድም በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

እረኝነት እና መጋቢነት

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

 

መጋቢነት 

 

 

የእግዚአብሔር ለህዝቡ መራራቱ የዛሬ አሊያም የቅርብ ጊዜ አይደለም። ከጥንትም የእግዚአብሔር ባህሪ ለሕዝቡ መራራቱ ነው። ምንም እንኳን አዳምና ሔዋን ከእግዚአብሔር ትዕዛዝ ፈቀቅ በማለት በመሸሻቸው እግዚአብሔር መጣራቱና መፈለጉ ምን ያህል እግዚአብሔር እጅግ ርኅሩህ መሆኑን፣ ለልጆቹም ምን መሐሪ መሆኑን ማወቅ እንችላለን። 

እግዚአብሔር ለሕዝቡ የሚቀና ለምድሩም የሚራራ አምላክ ነው። ይህ የእግዚአብሔር መለያውና የምህረቱ ባህሪው ነው። በተለይ ለኪዳኑ ህዝብ፣ ለጠራውና ለለየው ህዝብ የሚራራ ነው። ከመራራቱም በላይ አንድያ ልጁን መስጠቱ እንድንጠፋበት አለመፈለጉን መግለጫ ነው።

በዋናነት የእግዚአብሔርን ቃል መጽሐፍ ቅዱስን በጥልቀት በምናነብት ጊዜ እግዚአብሔር ምን ያህል ለሕዝቡ እንደተጨነቀና፣ በአገልጋዮቹም ተጠቅሞ ምን ያህል ለህዝቡ የእረኝነቱን ባህሪ እንዳሳየን በስፋት እንመለከታለን።

በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ በአብዛኛው የተገለጡት የእግዚአብሔር አገልጋዮች ምን ያህል በእግዚአብሔር እረኝነት ውስጥ ያለውን የእረኝነትን እሳቤ ተረድተው በሱ ልክ መጨነቃቸውን በውል መመልከት እንችላለን። በአብዛኛው በአገልግሎታቸው ውስጥ ለህዝብ መራራታቸው እግዚአብሔር በፈለገው ልክ ተረድተው አገልግሎታቸውን ሠርተው ፈጽመዋል።

እረኝነት ክርስቶስ የመጣበት ዋነኛ አላማው እንደነበረ፣ በተለይም በበረት ውስጥ ላሉት ብቻ ሳይሆን፣ ከበረት ውጭም ላሉት ጭምር የእረኝነቱ ጭንቀት ነበረ።

የእረኝነት ትልቁ ተልዕኮው አደራን ከመቀበል ጋር ተያይዞ አንድም መንጋ እንዲጎድል፣ አንድም መንጋ እንዲጠፋበት አይፈለግም፣ ይህም አይጠበቅበትም።

ብዙውን ጊዜ ችላ ባይ እረኞች፣ ኃላፊነትን እና አደራን ቸል በማለት እንኳን የጠፋውን በአጠገብ ያለውን ያጣሉ፣ ይጠፋባቸውማል።

ዛሬም በዘመናችን የምናያቸው አንድም በስም መሾም ግን በግብር፣ በምግባር፣ በሥራ ግን የማይገለጥ መጋቢ ተብሎ በመቀመጥ፣ መጋቢ ሳይሆኑ ተመጋቢ፣ አደላቢ ሳይሆኑ ደላቢ፣ አሰማሪ ሳይሆኑ ተሰማሪ፣የከሳውን ተመልካች ሳይሆኑ፣ መክሳታቸውን የሚመለከቱ፣ የተመረጠውን ለመንጋው ሳይሆን ለራስ መናኛውን ለመንጋው አቅራቢ በበዛበት ዘመን፣ የሰባውን መርጦ ተመጋቢ እጅግ የበዛበት ዘመን ቢኖር ይህ ዘመን ነው።

ዳዊት እንዲህ አለ፦ “እግዚአብሔር እረኛዬ ነው፥ የሚያሳጣኝም የለም።” — መዝሙር 23፥1። እግዚአብሔር እረኛውና እንደማያሳጣውም በውል ያወቀ ትልቅ የእግዚአብሔር ሰው፣ በዘመኑ የእግዚአብሔርን ሐሳብ አገልግሎ የኖረ፣ በምድረ በዳ የአባቶቹን በጎች ሲጠብቅ የኖረና፣ ድብና አንበሳ ግልገሎቹን ሲውድበት ተከታትሎ የሚናጠቅ፣ የነጠቁትንም ዳግም እንዳይመለሱ ገድሎ የሚመጣ በእርግጥም እረኝነት የገባውና የተረዳ ትልቅ መሪ፣ በምድረበዳ እግዚአብሔር ባለማመደው ህይወት ወገኑን ከጠላት እጅ ያስጣለ፣ ጎልያድን በአንድ ድብልብል ድንጋይ በእግዚአብሔር ስም የጣለ ትልቅ ለሐገሩ፣ ለሕዝቡ፣ ለእምነቱ፣ ለእግዚአብሔር ክብር እረኝነቱን የጀመረ አገልጋይ ነው። በዚህ እውነታና መረዳት ውስጥ ካልገባን እረኝነት እጅግ ከባድ ነው። “በትሩንም በእጁ ወሰደ፥ ከወንዝም አምስት ድብልብል ድንጋዮችን መረጠ፥ በእረኛ ኮረጆውም በኪሱ ከተታቸው፤ ወንጭፍም በእጁ ነበረ፤ ወደ ፍልስጥኤማዊውም ቀረበ።” — 1ኛ ሳሙኤል 17፥40።

 

መንጋን ለይቶ ማወቅ 

 

 

እረኛና መንጋ አብረው ለመቆየት የእርስ በእርስ መተዋወቅ፣ ድምፅን መለየት፣ መልክን ለይቶ ማወቅ እና መተዋወቅ የግድ ነው። “መልካም እረኛ እኔ ነኝ፥ አብም እንደሚያውቀኝ እኔም አብን እንደማውቀው የራሴን በጎች አውቃለሁ የራሴም በጎች ያውቁኛል፤ ነፍሴንም ስለ በጎች አኖራለሁ።” — ዮሐንስ 10፥14-15።

መንጋን ለይቶ ማወቅ የእረኛ ትልቁና ዋነኛ ተግባሩ ነው። ምንም እንኳን አካላዊ ቁመና እና መልካቸው ለየቅል ቢሆንም የራስን መንጋ ለመለየት እጅግ ጠቃሚ ነው።

ዛሬ በዘመናችን ያሉ እረኞች ለቀረቧቸው አሊያም ያዋጡናል ብለው የሚያስቡትን እንጂ የደከመን፣ በማህበራዊም ይሁን በኢኮኖሚ አቋማቸው ዝቅ ያሉትን የደከሙትን ሲመለከቱ ሲጎበኙ አይታይም። ይህ ደግሞ የአንድ እረኛ ባህሪ ጨርሶ ሊሆን አይችልም። ለዚህ ነው በመንጋውና በእረኛው መሃል እጅግ የሰፋ ክፍተት የበዛው፣ ለቤተክርስቲያንም ተግዳሮት የሆነው። “መንጋውን ለሚተው ለምናምንቴ እረኛ ወዮለት! ሰይፍ በክንዱና በቀኝ ዓይኑ ላይ ይሆናል፤ ክንዱም አጥብቃ ትደርቃለች፥ ቀኝ ዓይኑም ፈጽሞ ትጨልማለች።” — ዘካርያስ 11፥17።

እረኛ የደከመን ካላየ፣ የከሳው ካልተመለከተ፣ የተጎዳን ካላበረታ የእረኝነቱ ትርጉም ይጠፋል። በሚገባው መልኩ ካላሰማራና ካልመሰገ የመንጋው ህልውና አደጋ ላይ ይሆናል። “እረኛንም በማጣት ተበተኑ፥ ለምድርም አራዊት ሁሉ መብል ሆኑ፥ ተበተኑም።” — ሕዝቅኤል 34፥5።

የዛሬ እረኛ እራሱን የሚያሰማራ እና የደለበውን ለራስ ጥቅም ከማዋል ባሻገር ለመንጋው ያውም ክርስቶስ ለሞተለት ህዝብ ግድ የሚለው የአደራ ሰው አይደለም፣ ከዚህም የተነሳ ለነጣቂ ተኩላ ተላልፎ በመሰጠቱ ቤተክርስቲያን አደጋ ተጋርጦባት በተግዳሮት ውስጥ ነች። “ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እኔ ሕያው ነኝና እረኛ ስለሌለ እረኞቼም በጎቼን ስላልፈለጉ እረኞችም ራሳቸውን እንጂ በጎቼን ስላላሰማሩ፥ በጎቼ ንጥቂያ ሆነዋልና፥ በጎቼም ለምድር አራዊት ሁሉ መብል ሆነዋልና”— ሕዝቅኤል 34፥8።

 

 

ባለቤትነትን በትክክል ማወቅ 

ብዙውን ጊዜ በዘመናችን የምንመለከተው መንጋን የመጠበቅና የመንከባከቡ ጉዳይ እጅግ በጣም የደከመ ከመሆኑ የተነሳ እንኳን በበረቱ ያሉትን ይቅርና አጠገብ በበረት አሉ ተብለው እንኳን የሚታሰቡት በትክክል በእንክብካቤ ሲያዙ አይታይም። መፅሐፍ ቅዱስ ግን ይህንን አይነግረንም። ጌታ ኢየሱስ ከተናገራቸው አብይ ንግግሮቹ በበረት ያልሆኑ፣ ከበረት ውጭ የሆኑ አሉኝ እያለ ሲናገር እንሰማለን። ስለዚህ በዘመናችን ያለን በእርግጥም በእረኝነት አለን ለምንል ይህ ቃል ሊገባን ይገባል። እረኝነት በእጅ ያለን ብቻ ሳይሆን ከእጅ ውጭ ያሉትንም ጭምር ይመለከታል። እያጎደሉ መሄድ ሳይሆን እየጨመሩ መሄድ ነው። እያጡ ሳይሆን እየተንከባከቡ መያዝና እየበዙ መሄድ ነው። በዚህ ቃል እውነታ ላይ መገአት ይሁንልን። “ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምፄንም ይሰማሉ፥ አንድም መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ።” — ዮሐንስ 10፥16። 

ምናምንቴ እረኛ

ምናምንቴነት ከባህሪ ባለፈ በተለይ ከግብር አንፃር እጅግ ጸያፍ የሆነ፣ እምነት የማይጣልበት፣ ለአደራ የማይበቃ፣ ለራስ ጥቅም ብቻ የሚኖርበት አመል ወይም ባህሪ ነው።

ምናምንቴነት እጅግ የወረደ፣ ጸያፍ ባህሪን ያዘለ የውርደትና የውድቀት ጥግ መገለጫና ማሳያ ው። ዛሬም በዘመናችን ባለች ቤተክርስቲያን ውስጥ ባሉ አገልጋዮች ዘንድ በውልና በግልፅ እየታየ ያለ ነው።

ምናምንቴ ሌላኛው መገለጫው በተለይም የከፋው መለያው እግዚአብሔርን አለማወቁ በተጨማሪም እግዚአብሔርን ጨርሶውኑ የማይፈሩ ደፋርና የመሠላቸውን ከማድረግ የማይመለሱ፣ የእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ቦዘኔዎች (ይቅርታ) ናቸው።

ምናምንቴዎች ለአደራ የማይበቁ ታማኝነት የጎደላቸው ሰዎች ናቸው። በተለይ ጉባኤን የሚያነውሩ እና የሚያስነውሩ ናቸው። “ዔሊም እጅግ አረጀ፤ ልጆቹም በእስራኤል ሁሉ ላይ ያደረጉትን ሁሉ፥ በመገናኛውም ድንኳን ደጅ ከሚያገለግሉት ሴቶች ጋር እንደ ተኙ ሰማ።” — 1ኛ ሳሙኤል 2፥22። “ልጆቼ ሆይ፥ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ኃጢአተኛ በማድረጋችሁ ስለ እናንተ የደረሰኝ ወሬ መልካም አይደለምና ይህ አይሆንም።” — 1ኛ ሳሙኤል 2፥24። “መንጋውን ለሚተው ለምናምንቴ እረኛ ወዮለት! ሰይፍ በክንዱና በቀኝ ዓይኑ ላይ ይሆናል፤ ክንዱም አጥብቃ ትደርቃለች፥ ቀኝ ዓይኑም ፈጽሞ ትጨልማለች።” — ዘካርያስ 11፥17።

ሰነፍ እረኛ 

 ሰነፍ ለአደራና ለቁምነገር ጨርሶ የሚሆን፣ ሊሆንም የማይችል ነው። ሰነፍ በባህሪው እያወቀ እያወቀ በቸልተኝነት፣   እየገባውም ቢሆን በምን አለብኝነትና በምንአገባኝ የሚንቀሳቀስ ነው። አይቶ እንዳላየ፣ ሰምቶ እንዳልሰማ በመሆን የሚኖር ሲሆን በጥቅሙ ረገድ ግን የራሱን አስጠብቆ የሚኖር ነው። እራሱን ከማሰማራት ወጭ ሌላውን "በለመለመ መስክ" አያውልም አያሰማራም። መንጋውን ተገቢ በሆነ መልኩ አይመስግም፣ ወደየት እንደሚመስግም ጨርሶ አያውቅም። ለሌላው ግን ግድ የሌለው፣ ለስልጣንና ለስም ብቻ ነገሩን፣ ጥቅሙን አስጠብቆ የሚኖር ነው።

ዛሬም በዚህ በድህረ ዘመን በስልጣኔ ሁሉ በረቀቀበት ዘመን ያሉ በስም የተካቡ፣ በስም የተተበተቡ፣ በዝናና በታዋቂነት የተጠነዙ ግን የሚታይ የተገለጠ፣ የሚዳሰስ የተጨበጠ፣ የሚሰማ የሚቀር የማይረሳ ነገር የሌላቸው በበዙበት በዚህ ዘመን ባሉ አገልጋዮች የአህዛብ መሳለቂያ እና መሰደቢያ የሆንነው።

የዛሬ አገልጋይ ስንፍና የማይከሳቸው፣ በሥራ የማያምኑ፣ ግን ጥገኛ ሆነው ተመፅዋች፣ ተሠፋሪ ግን የማይሠፍሩ፣ ሁሌም እንደተሰፈረላቸው የሚኖሩ፣ መንጋን እያከሱ ራሳቸው የሚደልቡ አሁን ግን አይሆንም። ከኃላፊነት መነሳት፣ የሹመቱም ምልክት መገለጫ ይወሰድበታል። የማዘንና የመራራት ልብ የላቸውም። “እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፦ ዳግመኛም የሰነፍን እረኛ ዕቃ ውሰድ።” — ዘካርያስ 11፥15።

 ሞያተኛ እረኛ

በእረኝነት ደረጃ ብናየውና ብንመለከተው እረኛ ነው ሆኖም ግን የባለቤትነት ስሜት ጨርሶውኑ የለውም፣ የባለቤቱን ያህል ምንም ነገር አይሰማውም።

ሙያተኛ እረኛ ሊመግብ፣ ሊያበላ፣ ሊያጠጣ ይችላል ከአጥፊ ጠላት ግን አይከላከልም አያስመልጥም፣ አያተርፍም። ለትውልድና ለተተኪ ጨርሶውኑ ግድ የለውም። የኃላፊነትና የተጠያቂነት ስሜት የለውም። ሙያተኛ እረኛ የተሻለ ነገርና ጥቅም ካገኘ ቀድሞ የነበረበትን ለቅቆ ለራሱ ጥቅም የሚበጀው ላይ ለሥራት ትቶ የሚሄድ ነው፣ ሙያተኛ የተቀጣሪ ያህል ስሜት ያለው ነው።ምክንያቱም የባለቤትነት ስሜት የለውምና። ለራሱ የሚፈልገውን ከአጣ ለሌላው ግድ አይለውም። አዛኝ፣ የሚራራ ልብ የላቸውም። ጌታችን ኢየሱስ እንዳደረገው "ነፍሱን ለወዳጆቹ አሳልፎ እንደሰጠ" ይህን አይነት ትልቅ አደራ የለውም። “እረኛ ያልሆነው በጎቹም የእርሱ ያልሆኑ ሞያተኛ ግን ተኵላ ሲመጣ ባየ ጊዜ በጎቹን ትቶ ይሸሻል፤ ተኵላም ይነጥቃቸዋል በጎቹንም ይበትናቸዋል።” — ዮሐንስ 10፥12።

የሚያዝን ልብ

ትክክለኛ እረኛ በባህሪው የሚያዝን ልብ ያለው ነው፣ አይቶ ዝም የሚል አይደለም፣ በስጋም ቢሆን በመንፈሳዊ ነገር ይመግባል፣ ያስተምራል። በአብዛኛው በመንፈሳዊ ነገር መግቦቱ ትልቅ ነው፣ ምክንያቱም የመጣበት አላማ ህዝብን አጠፋበት ከእግዚአብሔር እቅፍ መልሶ ወደ እግዚአብሔር እረኝነት ወደ በረቱ የሚመልስ ነው፣ ለመንጋው ይጨነቃል።

ትክክለኛ እረኛ ልቡ የሚያዝን፣ የትና መች እንደሚያሰማራ እና እንደሚመስግ በትክክል በውል ያውቃል። በቀን ወዴት እንደሚያሰማራ፣ በለሊት ወዴት እንደሚመስግ ያውቃል። እራሱን ለማሰማራት አይጨነቅም፣ አብሮ ግን ወዴት እንደሚሰማራ ያውቃል። ከመንጋው አይርቅም፣ አብሮነቱ የሁልጊዜ ነው። “ኢየሱስም ወጥቶ ብዙ ሕዝብ አየና እረኛ እንደሌላቸው በጎች ስለ ነበሩ አዘነላቸው፥ ብዙም ነገር ያስተምራቸው ጀመር።” — ማርቆስ 6፥34። “እርሱ ግን መልሶ፦ እናንተ የሚበሉትን ስጡአቸው አላቸው። ሄደን እንጀራ በሁለት መቶ ዲናር እንግዛላቸውን? እንዲበሉም እንስጣቸውን? አሉት።” — ማርቆስ 6፥37። “ሁሉንም በየክፍሉ በለመለመ ሣር ላይ እንዲያስቀምጡአቸው አዘዛቸው።” — ማርቆስ 6፥39።

በባለቤቱ ልክ አደራን መወጣት

ዛሬ በዘመናችን ከምናየው በጥቂቱ ትላንት አንቱ የተባሉ፣ አብረውን ሲያመልኩ እና ሲያገለግሉ የነበሩ ዛሬ ግን በአለም ያሉ በሞት መንገድ በሰፋው እንዳሻቸው እየሆኑ ያሉ፣ ትላንት ፈሪሃ እግዚአብሔር የነበራቸው ዛሬ ግን የአለምን ነገር ጭልጥ ብለው ገብተው የሚጨልጡ፣ እንዲህ የመሆናቸው ዋናው ምክንያት አንድም በሰነፍ እረኛ ሁለትም በሙያተኛ እረኛ ሶስትም በምናምንቴ እረኛ እንደሆነ ግልጽ ነው። ምክንያቱም አደራ በሰጠው በክርስቶስ ልክ ካለመወጣት የተነሳና፣ አደራ ሰጪውን ካለመውደድ የተነሳ ነው። የዛሬ ዘመን እረኛ እንኳን ለደካማው ለበረታውም ክርስቲያን መውደቂያ እና አንገት መድፊያ ሆነዋል። “ምሳ ከበሉ በኋላም ኢየሱስ ስምዖን ጴጥሮስን፦ የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ ከእነዚህ ይልቅ ትወደኛለህን? አለው። አዎን ጌታ ሆይ፥ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ አለው። ግልገሎቼን አሰማራ አለው።”— ዮሐንስ 21፥15።

“ደግሞ ሁለተኛ፦ የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ ትወደኛለህን? አለው። አዎን ጌታ ሆይ፥ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ አለው።” — ዮሐንስ 21፥16። “ደግሞ ሁለተኛ፦ የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ ትወደኛለህን? አለው። አዎን ጌታ ሆይ፥ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ አለው።” — ዮሐንስ 21፥16። “መንጋውን ለሚተው ለምናምንቴ እረኛ ወዮለት! ሰይፍ በክንዱና በቀኝ ዓይኑ ላይ ይሆናል፤ ክንዱም አጥብቃ ትደርቃለች፥ ቀኝ ዓይኑም ፈጽሞ ትጨልማለች።” — ዘካርያስ 11፥17።

የተነሱ እረኞች ግን ለኃላፊነት የማይበቁ

ምንም እንኳን እግዚአብሔር በጸጋው ስጦታ ባይፀፀትም፣ ብዙዎች ግን በመልካም አነሳስ ቢነሱም፣ አገልግሎታቸው ለሁሉም ተደራሽ ቢሆንም አብዛኞቹ አጀማመራቸው ላይ እንደነበረው እያስኬዱ ባይሆንም፣ እንደጀመሩት ሳይሆን የጠፉም እንዳሉ የማይደበቅና የማይካድ የማይታበል ሐቅ ነው።

ብዙዎች በንዋይ መታለል፣ በባለጠግነት ምኞት መዋጥ፣ የትላንት መነሻ ህይወትን ጨርሶ መርሳት፣ በሌሎች ከፍታ ምኞት መታለል ባመጣው ጣጣ የቀድሞን የአገልግሎት ፍቅር ችላ በማለት ከዳር ሳያደርሱ ሩጫቸውን በመንገድ በመሐል ያቆሙ እጅግ አያሌዎች ናቸው። በተለይ በአይን አምሮት ተጠምደው የከበረ አገልግሎታቸውን ወደጎን ያደረጉ ብዙዎች ናቸው። ይማርካሉ ተብለው የታሰቡ ተማርከው የተገኙ የቀሩ ብዙዎች ናቸው። “እነሆ፥ በአገሩ ውስጥ እረኛ አስነሣለሁ፤ እርሱም የጠፋውን አያስብም፥ የባዘነውን አይፈልግም፥ የተሰበረውን አይጠግንም፤ የዳነውንም አይቀልብም፥ ነገር ግን የሰባውን ሥጋ ይበላል፥ ሰኰናውንም ይቀለጣጥማል።” — ዘካርያስ 11፥16።

ኃላፊነት እና ተጠያቂነትን የሚያውቅ እረኛ

እረኛ ለቅጽበትም ቢሆን እይታው አንድም በመንጋው ሁለትም ለመከላከል በነጣቂ አውሬ ላይ መሆኑ የግድ ነው። በተለይ ቀድሞ ለመከላከል ያመች ዘንድ በርቀትም ቢሆን ያለን ነጣቂን በጥንቃቄ ለመከላከል ያመች ዘንድ የማይዘናጋ ነው። ይህም የመልካም እረኛ መለያ ባህሪውና የተጠያቂነትና የኃላፊነት ስሜት በውስጡ ያለበት የእውነኛ እረኛ ባህሪ ነው።

እውነተኛ እረኛ በቃ መንጋዬ በአውሬ ተወሰደ ብሎ ዝም የሚል አይደለም፣ ተከትሎ የሚያስጥል፣ አስጥሎም የነጠቀውን አውሬ ዳግም ላይመለስ መትቶ ገድሎ ይመለሳል። “ዳዊትም ሳኦልን አለው፦ እኔ ባሪያህ የአባቴን በጎች ስጠብቅ አንበሳና ድብ ይመጣ ነበር፥ ከመንጋውም ጠቦት ይወስድ ነበር።” — 1ኛ ሳሙኤል 17፥34። “በኋላውም እከተለውና እመታው ነበር፥ ከአፉም አስጥለው ነበር፤ በተነሣብኝም ጊዜ ጕሮሮውን ይዤ እመታውና እገድለው ነበር።” — 1ኛ ሳሙኤል 17፥35። ለዚህ ነው ዳዊት፦ ይናጠቅ የነበረ፣ ያስጥል የነበረ፣ ያተርፍ የነበረ፣ በላተኛውን ይገድል የነበረ።

ትክክለኛ እረኛ ለወደፊቱም ይጨነቃል

ትክክለኛ እረኛ አደራውን በሰጠው ልክ የሚረዳና መጋቢነቱን በትክክል የሚከውን ነው። ምንም እንኳን አገልግሎቱን እና ሩጫውን ቢጨርስም፣ ለቀጣዩ ትውልድ አደራውን አስቀጥሎና አሸክሞ የሚሄድ የሚሰናበት ነው። በሜዳ በትኖ የሚሄድ አይደለም። አደራን እንደተቀበለ አደራን ሰጥቶ የሚሰናበት ነው። የጀመረውንና የተሰጠውን አደራ በመልካም አጨራረስ የሚያጠናቅቅ ነው። በተለይም እጅግ በማስጠንቀቂያ ምን ማድረግ እንዳለባቸውና ምን መጠንቀቅ እንዳለባቸው ጭምር በመንገር ይለያል። በተለይ በመካከላቸው ምን እና ማን እንደሚነሳ ጭምር እንዲነቁ አድርጎ ይሰናበታል። የጥንቃቄ አመላካች ሐሳብን ይጠቁማል። “ከሄድሁ በኋላ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች ተኩላዎች እንዲገቡባችሁ፥ ደቀ መዛሙርትንም ወደ ኋላቸው ይስቡ ዘንድ ጠማማ ነገርን የሚናገሩ ሰዎች በመካከላችሁ እንዲነሡ እኔ አውቃለሁ።” — ሐዋርያት 20፥29-30።

ትክክለኛ እረኛ ለመንጋው ይጨነቃል

 “ከጥቂት ቀንም በኋላ ጳውሎስ በርናባስን፦ ተመልሰን የጌታን ቃል በተናገርንበት በየከተማው ሁሉ ወንድሞችን እንጐብኛቸው፥ እንዴት እንዳሉም እንወቅ አለው።” — ሐዋርያት 15፥36። ሐዋርያው ጳውሎስ ካሉት ሐዋሪያት አንድ የሚለይበት ባህሪ በተለይ በአገልግሎቱ አንዴ ወንጌልን የነገራቸውን ሲተው የምናየው አገልጋይ አይደለም። በመጎብኘት ባህሪው የሚለይና የሚታወቅ ነው። አብያተክርስቲያናትን ያጸና የነበረ፣ የእግዚአብሔርን ምክር ሁሉ የሚናገር እንደነበረ የእግዚአብሔር ቃል ይነግረናል። “የእግዚአብሔርን ምክር ሁሉ ነግሬአችኋለሁና፥ ምንም አላስቀረሁባችሁም።” — ሐዋርያት 20፥27። “አብያተ ክርስትያናትንም እያጸና በሶርያና በኪልቅያ ይዞር ነበር።” — ሐዋርያት 15፥41።

ይህ ነው የትክክለኛ መጋቢ ባህሪ፣ ምንም እንኳን አገልግሎቱን፣ ሩጫውን ቢጨርስም ሌሎች እንዲቀጥሉ ምን ማድረግ እንዳለባቸው እና የቀጣዩን ዘመን አገልግሎት በምን መልኩ መከወን መተግበር እንዳለባቸው ጭምር በአጽንዖት ይነግራቸዋል፣ ያስቀጥላልም። “በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ።” — ሐዋርያት 20፥28።

እነዚህን ወሳኝ ነገሮች ልብ ልንል ይገባል፦ የቤተክርስቲያን መጋቢ ማለት በእግዚአብሔር የተመረጠ፣ የክርስቶስን መንጋ፣ ምእመናንን በመመገብ፣ በመጠበቅ፣ በመምራት እና በመንፈሳዊ ዕውቀት በማነጽ በቤተክርስቲያን ውስጥ ኃላፊነት የሚወጣ መንፈሳዊ መሪ ነው። መጋቢዎች የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት በማስተማርና መልካም ምሳሌ በመሆን ምእመናን በመንፈሳዊ ሕይወት እንዲያድጉ ይረዳሉ።

ዋና ዋና ተግባራት እና ባህሪያት፡

1- መንጋውን መመገብ፦ የእግዚአብሔርን ቃል በማስተማርና በመስበክ ምእመናንን በቅዱሳት መጻሕፍት መመገብ።

2- መጠበቅና መምራት፦ መንፈሳዊ ጥበቃ ማድረግ፣ መምከር፣ መገሰጽና ሕይወታቸውን በእግዚአብሔር መንገድ መምራት።

3- አርአያነት (መልካም እረኛ)፦ እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ ፍቅር፣ ትሕትና እና ታማኝነት በማሳየት ለአርአያነት ማብቃት።

4- ባህሪ፦ 1ኛ ጢሞቴዎስ 3:1-7 ላይ እንደተጠቀሰው የማይነቀፍ፣ በዕውቀት የጎለመሰ፣ አስተዋይ እና ቤተሰቡን በአግባቡ የሚመራ መሆን አለበት።

በአጠቃላይ፣ መጋቢ ማለት የእግዚአብሔርን ቤተክርስቲያንን በማስተዳደርና ምእመናንን በማገልገል ላይ ያለ፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መስፈርቶችን የሚያሟላ መሪ ነው።

በመጨረሻም፦ ትክክለኛ፣ እውነተኛ፣ መልካም እረኛ ለበጎቹ ድምጹን እንጂ በያዘው በትር ሲመታ አይታይም፣ ባይሆን ሙሴ በበትሩ እንደተጠቀመ ይጠቀምበታል እንጂ መንጋውን መደብደቢያ አሊያም መምቻ አድርጎ አይጠቀምበትም። ግራኙ ናኦድ በደበቃት ሰይፍ ለጠላቱ እንደተጠቀመ የመንጋውን ጠላት ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ የሚመታበት ነው።

ሰናይ ዘመን ይሁንልን!

ወንድም በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

እስክንድሮሶች

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

እስክንድሮሶች


የእውነት እና የሐቅ ተፃራሪዎች፣ በሐሳብ ሙግት ሳይሆን የሚጠሉትን በያዙት አቋምና እምነት የማይሟገቱ፣ ይልቁኑ በተቃውሞና በማጥላላት ላይ ተጠንዘው የሚገኙ፣ እውነትን እድሜ ሚያሳጥሩ የመሰላቸው፣ የሚቃወሙትን ግን እያጠነከሩት እንደሆነ የማይገባቸው፣ የራሳቸውን በአግባቡ ሳያውቁ የሌላውን እውነት ለማደብዘዝ፣ አዚም የሚያደርግ ባልጠፋበት #የዘመኑ_አዚመኞች፣ ግን ሳያውቁት ሌላውን እያጠነከሩ ያሉ #የዘመኑ_አስክንድሮሶች መኖራቸውን ለቅፅበት መዘንጋት የለብንም። ከሚቃወሙ የሚያነጥሩት ነሐስ አዋጪ መሆኑን ቢረዱ ምን ያህል መልካም ነበር? ምን ያህል ትርፋማ ይሆኑ ነበር። በተለይ የወንጌልን እውነት ይዘው እና አንግበው የሚንቀሳቀሱትን፣ በዘመኑ ላይ እየሆነ ያለውን ኢ-መፅሐፍ ቅዱሳዊ አስተምሮቶችን ነቅሰው በማውጣት እውነታውን ፍንትው አድርገው ገልጠው እና ገልጸው የሚያስተምሩትን በትችት ናዳ ለማሸማቀቅ የሚታትሩ #የዘመኑ_አዚሞች_አዚመኞች እነ #እስክንድሮስ እንዳሉ መረዳቱ እጅግ ጠቃሚ ነው። 
“የናስ አንጥረኛው እስክንድሮስ እጅግ ከፋብኝ፤ ጌታ እንደ ሥራው ይመልስለታል።” — 2ኛ ጢሞቴዎስ 4፥14።
የእግዚአብሔርን እውነት ይዘው እውነት እንድትታይ ሌት ተቀን ለምትታትሩ የእውነት ታጋዮች የሙግት ጊዜ ባይኖረን ግን እውነትን በፍቅር በመያዝ እና እየገለጥን መኖሩ ተገቢ ቢሆንም #ከእስክድሮስ መጠበቁ ግን እጅግ ጠቃሚ ነው። #እስክንድሮስ ከተቃውሞ ውጭ እንደማይሆን ማወቁም ተገቢ ነው። “አንተም ደግሞ ከእርሱ ተጠበቅ፥ የምንናገረውን እጅግ ተቃውሞአልና።”— 2ኛ ጢሞቴዎስ 4፥15። 

#የእነ_እስክድሮስ አቅማቸውም አቋማቸውም ተቃውሞ መሆኑ ሳይዘነጋ የተሰጠንን ሥራችንን እየሠራን መቀጠሉ እርሱ ዋናው ነገር ሲሆን ቦታም አለመስጠቱ እጅግ ተገቢ ነው። #እስክንድሮስ ጊዜን አባካኝ መሆኑን አለመርሳቱ ተገቢ ነው። ክርክር ጊዜና ዕድል መስጠት መሆኑን ለአፍታ_ለቅፅበት መዘንጋት የለብንም። ሥራው የተማርነውን እና የምናስተምረውን ትምህርት እግር በእግር የሚቃወም መሆኑን መዘንጋት የለብንም።
“ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ እናንተ የተማራችሁትን ትምህርት የሚቃወሙትን መለያየትንና ማሰናከያን የሚያደርጉትን ሰዎች እንድትመለከቱ እለምናችኋለሁ፥ ከእነርሱ ዘንድ ፈቀቅ በሉ፤” — ሮሜ 16፥17።

#እነ_እስክንሮስ በክርስቶስ ትምህርት የማይኖሩ አምላክ የሌላቸው መሆኑን ማወቁ ተገቢ ነው፣ ተቃውሞአቸውም ይህ ነው። በክርስቶስ ትምህርት ኖረው አምላክ ያላቸውን በማሳት የተካኑ መሆናቸውን ማወቁ ተገቢ እና ወሳኝ ነገር ነው። 

መፍትሄው
1-
መጠበቅ
2-
ፈቀቅ ማለቱ ተገቢ ነው።

ሰናይ አገልግሎት እና ዘመን ይሁንልን!

ወንድም በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

ዲዮጥራጢስ

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

ዲዮጥራጢስ


በመልዕክተኛው በዮሐንስ ዘመን በቤተክርስቲያን የነበረ ዋነኛ ሆኖ መታየትን የሚፈልግ፣ የእውነትና የእውቀት ጠላት የሆነ፣ እውነትን ይዘው ለሚጓዙ ዕንቅፋት፣ እውነትን አንግበው ለሚፈጥኑ ትክል ድንጋይ፣ ለቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ግድ የሌለው፣ ዳሩ ግን ዋናቸው ሊሆን የሚወድ የስልጣን ጥመኛ፣ እውነትን አንግበው የሚሄዱትን የማይቀበል፣ የመጣውን በክፉ ቃል በመለፍለፍ የሚነቅፍ (ያልተጎሰመ_አንደበት_አንጋቢ)፣ ለወንድሞች ቦታ የሌለው፣ የማይቀበል፣  ሌሎችን በማሳመፅ እውነትን የያዙትን እንዳይቀበሉ የሚያደርግ፣ ከትዕዛዙ የወጣውን ከቤተክርስቲያን የሚያስወጣ፣ የሚያሸሽ ዛሬም በአጠገባችን፣ በዙሪያችን ያሉ አይደሉምን?

ለጋይዮስ እና ለድሜጥሮስ፦ በመልካም የሚሄዱትን፣ በሁሉ ዘንድ በመልካምነት የሚመሰከርላቸው አጠገብ የማይጠፋ ድዮጥራጢስ፣ ዛሬስ የሉምን? እጅግ በቁጥር በዝተው፣ ከፍታውን ይዘው፣ ከጨለማው አለም ሰራተኞች በላይ ተግተው የሚሠሩ ዛሬም አሉ። ስውር ሥራ፣ ስውር ደባን እንደ አዳኝ አድፍጠው የሚከውኑ፣ ሁሉን ተቆናጥጠው የሚሠሩ ዛሬም አሉ። ርቀው የማይሄዱ የወዳጅ ጠላት እነ አኪጦፌል ዛሬም አሉ። የጥንቱ አኪጦፌል መልኩን ቀይሮ የመጣ ዲዮጥራጢስ እሱ ሳይሆን ይቀር? የድሮ ሰይጣን ዛሬም እሱ ነው። የተሸነፈ ግን ነው!

እነ ዲዮጥራጢስን እንጠንቀቃቸው። ሁሌም አጠገባችን አይታጡም። ትንሿን መልካም ነገር እንዳንሰራ ነገሮችን ያበላሻሉ፣ ያጠፉብናልም።

ይህን ማወቅ እና መረዳት ይሁንልን

“ሥራ የሞላበት ትልቅ በር ተከፍቶልኛልና ተቃዋሚዎችም ብዙ ናቸው።”— 1ኛ ቆሮንቶስ 16፥9።
“
በአንድም ነገር እንኳ  በተቃዋሚዎች_አትደንግጡ፤ ይህም ለእነርሱ የጥፋት፥ ለእናንተ ግን የመዳን ምልክት ነው፥ ይህም ከእግዚአብሔር ነው፤” — ፊልጵስዩስ 1፥28።

ዲዮጥራጢስ ድጡ ለአንተ!

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደሙ ይሰውረን!

ወንድም በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

የተፅእኖ ሰው

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

የተፅእኖ ሰው

እነርሱ በእምነት መንግስታትን ድል ነሡ ጽድቅን አደረጉ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ

                                                       ዕብራውያን 11፡33

በምድራችን ላይ በየትኛውም ዘመን በታሪክ መዛግብት እና በአፈ ታሪክ እንደሚነገረን፣ ከኖርንባቸው ዘመናት ቀድመው የኖሩ በፍልስፍናቸው አመለካከት ይሁን፣ በÞለቲካ አመለካከታቸውና ፍልስፍናቸው ይሁን፣ በፈጠራ ሥራና ግኝት ልህቀት ይሁን፣ ብቻ በተሰማሩበት በየትኛውም ዘርፍ ተፅዕኖን ፈጥረው ለዓለም የሚጠቅም አዎንታዊ ይሁን፣ የማይጠቅም አሉታዊ ጉዳይ ይሁን ሰርተው አልፈዋል፣ አንቱታንም ተችረው፣ ተሞግሰው ለበጎ ነገር ይሁን ለዕኩይ አንድ አሻራ ጥለው አልፈዋል፡፡

በክርስትና እምነት መፅሐፍ ቅዱሳችን እንደሚነግረን በምድር ላይ ተፅዕኖን ፈጥረው የኖሩ ሰዎች እጅግ ብዙዎች ሲሆኑ ተፅዕኖ ብቻም አይደልም ተፅዕኖ ፈጥረው የኖሩበትን አሳይተውና ገልፀው፣ አስከብረው  ኖረው አልፈዋል፡፡

የሰው ልጅ በዘመኑ በተለይ በኖረበት ዘመን ባለበት አካባቢ አንድ የማይረሳ አሻራን ጥሎ ማለፍ የግድ ነው፡፡ ይህም ሲባል ከላይ በአለም ካሉ ሰዎች ዘንድ በተነገረ የተፅዕኖ ሰውነት ዝርዝር ቢታይም በእኛ እግዚአብሔርን እናመልካለን በምንል እና ክርስቲያኖች ነን ብለን እራሳችንን የለየንና ሌሎችም የሚያውቁን በዘመናችን እንደ ቀደሙት አባቶች በዘመናችንና በኖርንባቸው ማህበረሰቦች ዘንድ እንደ ቀደሙት የእምነት አባቶች አንድ ተፅዕኖ ፈጥረን የፈጠርንበትንም አሳይተን፣ አሳውቀን ማለፍ የግድ ነው፡፡

በተለይ በዚህ ዘመን ያለን የወንጌል አማኞች ነን ብለን የምንናገር፣ በሌሎችም ዘንድ እሱ እኮ፣ እሷ እኮ ክርስቲያን ነች፣ አማኝ ነው ተብለን ምንታወቅ በተቃራኒው ግን በሌላ መልክ የምንታወቅ ብዙዎች ነን፡፡ ለያዝነው ወንጌል እውነት እንደሚገባ የማንኖር፣ የኖረውንም የምናስተች እጅግ አያሌ ሰዎች መሆናችን የገሃዱ አለም ሃቅ ነው፡፡ ሊያገለግሉ ለቆረጡ ሰዎች የመሰናክል እና የእንቅፋት ድንጋይ በመሆን ለአለም እና ለሰይጣን መንግስት ደጋፊ ሃሰብ አቅራቢዎች መሆናችን እጅግ ለእግዚአብሔር መንግስት ሳንካዎች ሆነናል፡፡

የእግዚአብሔር ልጅ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዋጋ የከፈለበትን ትልቁን የክርስትና እምነታችን በጥቂቶች አይደልም፣ በበዙቱ ስህተት ሲተች፣ ሲነቀፍ ይታያል፡፡ የቀደሙት የወንጌል አርበኞች የረሳቸውን ጥቅምና ዝና ትተው ወደ ኋላ አድረግው አይበልጥብንም የራሳችን ጉዳየው በማለት ዋጋ ከፍለውበት፣ እምቢ አሸፈረኝ ሰውን አንሰማም የሰማዩን እግዚአብሔር ብቻ ሰምተን ነው ምናገለግለው ብለው ዘመናቸውን የሰጡበትን፣ መንግስታትን እምቢ ማለታቸው ለወንጌሉ እውነትና ሀቅ ላመኑበት ይህ ነው ማይባል እና የማይገመት ዋጋ ከፍለው ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስ አስከብረው አልፈዋል፣ ማለፍ ብቻ አይደለም የማይሻርና የማይረሳ ተፅዕኖን ፈጥረው አልፈዋል፡፡

የተፅዕኖ ሰዎች

1.  በራሳቸው ላይ ወስነው የወጡ ናቸው- ሙሴ

የአርባ አመት የምቾትና የድሎት ዘመንን እምቢኝ ይበቃኛል በማለትና ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራን መርጦ፣ ብድራቱንም ትኩር ብሎ በመመልከት ወስኖ መውጣቱና የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ ከኮሬብ ተራራ ጀምሮ በመቀበል፣ እግዚአብሔር ወደ ፈርኦን ቤት ልኮት በእግዚአብሔር ላይ በመታመን፣ ድምፁን ተቀብሎ እግዚአብሔር እንዲህ ይልሃል ያገለግለኝ ዘንድ ሕዝቤን ልቀቅ ይልሃል የሚለውን መልዕክት በመያዝ መውጣቱ በእግዚአብሔር ላይ ያለው የፀና እምነቱ የንጉስን ቤት ባለመፍራት በእግዚአብሔር ላይ ያለው እምነቱ ንጉስን እጅ እስከሚያሰጥ ድረስ አድርሷል፡፡

ማንነቱን ሲያውቅና ሲገባው፣ የራሱ ወገን ያልሆነን ሲረዳ፣ የራስ ሃገር እንዳልሆነ፣ የኪዳንና የአባቶቹ መሬትና ሃገር እንዳልሆነ ሲገባው፣ ዝርያው ከዛ እንደማይመዘዝ ሲያውቅ የራሱን ህዝብ በእግዚአብሔር ምሪት ነፃ ሊያወጣ የቻለ፣ በእግዚአብሔር ላይ በመታመን የተፅዕኖ ሰው በመሆን ትልቅ የእግዚአብሔርን ሥራ ሰርቶ ትውልድን ወደ ኪዳን ምድር መርቷል፡፡

2.  ጊዜያቸውን በአግባቡ የተጠቀሙ ናቸው- ዳዊት

ዳዊት የልጅነት ሕይወቱ በምድረ በዳ ቢያሳልፍም እግዚአብሔር በዛ ቦታ የወደፊት ኑሮውን በሚገባ ያሰልጠነበት፣ ያስተማረበት፣ ብቁ እሰከሚሆን እና እግዚአብሔር ለራሱ አላማ እስኪጠራው ድረስ የቆየበትና የከረመበት ስፍራ ምድረበዳ ነው፡፡ በተለይ ከድብና ከአንበሳ ጋር በመታገል በጎቹን ሲያስጥል የሰለጠነበት መንገድ የወደፊቱን የሕዝብን ኃላፊነት፣ የሐገር ጉዳይን በኃላፊነት፣ የእምነቱን ጉዳይ እንዴት ከጠላትና ከባዕድ አካላት እንደሚጠብቅ ጭምር እግዚአብሔር ያሰለጠነበት መንገድ እጅገ አስገራሚ ነው፡፡ ከአባቱ በጎች ጥበቃ የተጀመረ ሕይወቱ፣ ለራስ ሳይሆን ለሌላ ወይም ለቤተሰቡ መኖሩ እንዴት ለሌላ መኖር እንደሚቻል ጭምር በሚገባ አሰልጥኖታል፡፡

ከዚህ ባለፈ ዳዊት በእግዚአብሔር ጥሪ መሰረት ለዓላማው ሲጠራው ዘመኑን በሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠትና ሃሳቡንም በማገልገል ዘመኑን ሰጥቶታል፡፡ በተለይ የልጅነት የምድረበዳ ህይወቱን ቀጥታ እግዚአብሔር በመጠቀም ዕድሜውን በሙሉ የእግዚአብሔርን ጦርነት ተዋግቶ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ከባዕዳን ሰዎችን  ነፃ በማውጣት እና እምነትንም በመጠበቅ በዘመኑ ሁሉ በድል ተመላልሷል፡፡ 

በተለይ ዳዊት ከሚለይባቸው ባህሪያት መካከል በየትኛውም ጦርነት እግዚአብሔርን ሳይጠይቅ የወጣበት ጦርነት የለም፡፡ እግዚአብሔርም ዳዊት በሔደበት ሁሉ ድልን ይሰጠው ነበር ሕዝብም በማሞገስና በመሸለል ውዳሴን ሲያቀርቡለት ነበር፡፡

ዳዊት መጠየቁ እግዚአብሔር ዋስትና እንዲወስድለትና እርግጠኛም ለመሆን እግዚአብሔርን አምኖ በመጠየቅ ይወጣ ነበር፡፡ የእግዚአብሔርን ሥራ በራስ እንደማይሰራ ዳዊት ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ የተፅዕኖ ሰው ማለት ተፅዕኖ እንዲያደርግ የሚያደርገውን እና የሚረዳውን ማወቅ ማለት ነው፡፡

3.  በዘመናቸው ላይ ተፅዕኖ ፈጥረው አልፈዋል

በመፅሐፍ ቅዱሳችን በቀደሙት አባቶች ዘንድ ገንኖ እና በዋናነት ይታይ የነበረው በእግዚአብሔርና በእግዚአብሔር ጉዳይ ላይ የማይደራደሩበት ነገር ትልቁና ዋነኛው በሕይወታቸው የሚታየው ነው፡፡ በተለይ በተፃራሪ መንገድ የእግዚአብሔርን ነገር በመቃረን የሚመጡትን በምንም አይነት መንገድና መልኩ አይታገሱበትም፣ በተቃራኒ በመቆም በእግዚአብሔር በመወራረድ በዘመናቸው ላይ የመጣውን ተግዳሮት ፊት ለፊት በመጋፈጥ ሲያጠፉትና ሲያስወግዱት ታይተዋል፡፡

ከሚገርመው ነገር አንዱ ብቸኛ መሆናቸውን ጨርሶ አያስቡትም፡፡ ከእኔ ጋር ያለው ከሁሉም ይበልጣል ማለት የየዕለት መርሃቸውና የእምነት መግለጫቸው ሲሆን በእግዚአብሔር ከአሸናፊዎች መብለጣቸው ትልቁ መፈክራቸውም ነው፡፡ 1ኛ ነገሥት 16፡31-33 የአክዓብን ታሪክና የኤልያስን ታሪክ በምንመለከትብት ጊዜ በተለይ አክዓብ በኪዳን ምድር ኢዮርብዓም በሄደበት ኃጢአት ሄዶ በተለይም ኤልዛቤልን ማግባቱ እና የበዓል ነቢያትን በገበታዋ መመገብዋ እና አክዐብን ማሳቷ ኤልያስ ሚጣገሰው ጉዳይ ባለመሆኑ በምድሪቱ ምንም አይነት ጠልና ዝናብ እንዳይዘንብ ማድረጉና እግዚአብሔር ሸሽጎት ሲመግበው ምን ያህል በዘመኑ ላይ በእግዚአብሔር ታምኖ ተፅዕኖ ማድረጉና እግዚአብሔር አስከብሮ ተፅእኖ ፈጠሯል፡፡

4.  ከራሳቸው በላይ ላመኑበት ኖረዋል

በተለይ ባመኑበትና በተማሩት የአባቶች መንገድ በተሰጣቸውም በህገ እግዚአብሔር ወደ ግራም ወደ ቀኝም ሳይሉ በእግዚአብሔር ሕግ መኖራቸው እግዚአብሔር እራሱ ከእነርሱ ጋር መሆኑን በትክክል አሳይቷል፡፡ በእግዚአብሔር ሕግ የሄዱ እና የኖሩ፣ ብሎም መንገዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር ያደረጉ በምንም አይነት መንገድ ውስጥ ሲያለፉም ይሁን በፈተና ውስጥ ሲያልፉ እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር ነበረ በድልም አልፈው በዘመናቸው ተፅዕኖን ፈጥረው እግዚአብሔርን ለሕዝብ አሳይተው የእነርሱ አምላክ በሀገር ይመለክ አሰኝተው አልፈዋል፡፡

በምርኮ የነበሩትና የንጉስ አርጤክስስ ሚስት በነበረችው በአስቴር ዘመን በህገ እግዚአብሔር በመመራት የኖሩትን አይሁድ ሓማ ሊያሰገድል በተሰናዳበትና ዝግጅቱን ባጠናቀቀበት ዘመን ንግስቲቱ የፆምና የፀሎት ጊዜን ለአይሁድ ማወጇ እና ወደ እግዚአብሔር መጮኋ ትልቅን የድል ብስራትን ማምጣቱና የታወጀውን አዋጅ ማስገልበጧ ሁሉን መቀየር ወደ ሚችለው ፊቷን ከህዘቧ ጋር ማዞሯ መልስን ከእግዚአብሔር አምጥቶላቸዋል፡፡ በመቶሃያ አገራት የአይሁድ አምላክ ይመለክ እንዲሉ ማድረጋቸው አንደኛው በእግዚአብሔር ላይ መተማመናቸውና ፀሎትን ሰምቶ ወደ ሚመልሰው መጮሃቸው ያመጣው ድልና የተፅዕኖ ሰው አድርጓቸዋል፡፡

በኃጢአት ላይ ባለ አመላካከት እጅግ የጸና አቋም በመያዝና ከእግዚአብሔር ጋር መልካም ግንኙነት፣ እግዚአብሔርን ማስቀደሙ ምንም እንኳን ፀሎት እንዳያደርግ በአዋጅ ቢከለከልም እግዚአብሔርን ማለቱ የዕለት ተግባሩ እና የማቋረጥ መሆኑ የገባው ዳንኤል በዘመኑ ላይ ተጽዕኖን በማምጣት እግዚአብሔር በምድር በመቶ ሃያ ሀገራት ላይ እንዲመለክ አድርጓል፡፡ በእግዚአብሔር ላይ መታመኑ ከአናብስት አፍ እግዚአብሔር ሲያድነው ሃገር ምድሩ ቢመለከትም ለዳንኤል ሲል ንጉሱ እንቅልፍ ማጣቱ ምን ያህል እግዚአብሔር ለዳንኤል እንደሚጨነቅለት አስረጂ ነው፡፡

እኛስ ዛሬ በዚህ ዘመን ያለን ክርስቲያኖች በእርግጥ በእግዚአብሔር ህግና ትዕዛዝ የእነርሱን ፈለግና አብነት ተከትለን ይሆን እየኖርን ያለነው?

5.  ለጥቅማቸው ሳይሆን ላመኑበት ጥቅም ኖረዋል- ደቀመዛሙርት ሁሉን ትተው

በሰው አሰራር የተጠሩበት ስፍራ በምንም መልኩ ለመመረጥ መስፈርት እና ቅድመ ሁኔታ ሊሆን ከማይችልበት ስፍራ የተጠሩት ደቀ መዛሙርት፣ ለጥሪው አፋጣኝ መልስ በመስጠት የተከተሉት፣ የያዙትና የነበራቸውን ነገር በመተው ጌታን ተከትለውታል፡፡ የሶሰት አመት ተኩል ከጌታችን ኢየሱስ ጋር መቆየታቸው ሊሰራቸውና ለአገልግሎት ሲያዘጋጃቸው ምን ያህል እግዚአብሔርን ማገልገል እንዳለባቸውም ጭምር አሰልጥኖአቸዋል፡፡ መሄድ ካስፈላጋቸው እንኳን ሲጠይቃቸው ከአንተ ወዴጥ እንሄዳለን አንተ የህይወት ቃል አለህ፣ ሁሉን ትተን ተከትለንሃል በማለት የቁርጠኝንትንና የውሳነየ ሃሳባቸውን ገልፀው የቀጠሉ፣ በአገልግሎት በዘመናቸውም ትልልቅ ተግዳሮትን ቢያልፉም ባሰለፋቸው እግዚአብሔር ላይ በመታመን፣ ምንም ማንንም ሳይፈሩ እኛ ግን የተሰቀለውን ክርሰቶስን እንሰብካለን፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትናም ዛሬም እሰከ ዘላለም ያው ነው በማለት ተፅዕኖን በወንጌል ኃይል በዘመናቸው ላይ ፈጥረው አልፈዋል፡፡

ዛርስ እኛ ክርስቶስን እንከተላለን የምንል በዘመናችን ላይ ክርስቶስን በመያዝ ጠፀዕኖን እየፈጠርን ነን?

6.  በእምነታቸው ተቃራኒ ከሆኑት ጋር ፊት ለፊት ተጋፍጠዋል

በነቢያት ዘመን ነቢያት ከሚያደርጓቸው አብይ ጉዳዮች መካከል በተለይ እግዚአብሔር ከሚጠላቸው ነገሮች ጋር አለመተባበር ሳይሆን ፈፅመው እነዚያን ነገሮች ከኪዳን ምድር ማጥፋታቸው ትልቁ ስራቸው ነበር፡፡ በምድራቸው እግዚአብሔር ብቻ እንዲመለክ፣ ሕገ እግዚአብሔር ብቻ በሕዝቡ ዘንድ እንደሚገባ እንዲተገበር ማድረጋቸው ከብዙ ስራዎጫቸው መካከል የሚጠቀስ ነው፡፡ በተለይ ኤልያስና የበዓል ነቢያት ያደረጉት ስራ እጅግ የሚገርም ነው፣ በተለይ ውርርዳቸው በአምለካቸው ላይ በመተማመን የሰሩት ስራ፣ የማን አምላክ ይበልጣል ብለው መፎካከራቸው፣ ኤልያስ በእግዚአብሔር ላይ ያለው መታመንና ንጉሱን ፈልጎ መገናኘቱ፣ ይባስ ብሎ የበዓል ነቢያት አራት መቶ ሓምሳውን መጥራቱ፣ የመሰዊያን ነቢያት አራት መቶውን መጥራቱ እና ከነዚህ ስምንት መቶ ሃምሳው ለባቻው ከአግዚአብሔር ጋር መጋፈጡ የሚያስገርምና በድል መመለሱ ትልቅ እምነቱ ነው፡፡

የእስራኤል መንግሥት በውሃ እጦት መቸገሩን ቀጠለ። ንጉስ አክዓብ ህዝቡ በኣል የሚባለውን የሀሰት አምላክ እንዲከተሉ ነገራቸው።1 ነገስት 18፥1–2፣ 17–18

እግዚአብሔር ነቢዩ ኤልያስ ከአክዓብ ጋር እንዲገናኝ ላከው። ኤልያስ ህዝቡን በሙሉ ወደ ተራራው ጫፍ እንዲመጡ ጋበዛቸው። እርሱም እግዚአብሔር እና ከበአል የትኛው እውነተኛ አምላክ እንደሆነ እንዲያዩ ንጉሱን እና ነቢያቱን ወደ ፉክክሩ ጋበዛቸው። 1ኛ ነገሥት 18፡19–21

ኤልያስ ፉክክሩን ገለጸ። እርሱ እና ካህናት ወይፈን በመሰዊያ ላይ ይሰዋሉ፣ ነገር ግን ራሳቸው እሳትን አያነዱም። ይልቁንም ካህናቱ እሳት ይለኩስ ዘንድ ወደ በኣል ይጸልያሉ። ከዚያም ኤልያስ እሳት ይለኩስ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ይጸልያል። ኤልያስ እውነተኛ አምላክ ብቻ እሳቱን እንደሚለኩስ ያውቅ ነበር።1ኛ ነገሥት 18፡22–25

 

የበኣል ካህናት ወደ አምላካቸው ከጠዋት እስከ ከሰዓት በኋላ ጸለዩ፣ ነገር ግን ምንም አልደረሰም። ኤልያስ ቀለደባቸው እናም አምላካቸው በኣል ተኝቶ ይሆናል አለ። 1ኛ ነገሥት 18፥26–27፡፡ ነቢያቱ ተናደዱ፣ በመሰዊያውም ላይ ዘለሉ፣ እናም እስከ ምሽት ፀለዩ። አምላካቸው መልስ ይሰጣል ብለው ተስፋ ነበራቸው፣ ነገር ግን ምንም እሳት አልነበረም። 1ኛ ነገሥት 18፥28–29፡፡ ከዚያም የኤልያስ ተራ ነበር። የጌታን መሰዊያ አበጀ፣ በመሰዊያውም ዙሪያ ጉድጓድ ቆፈረ፣ እንዲሁም መስዋዕቱን አዘጋጀ።1ኛ ነገሥት 18፥30–32

 

Description: ኤልያስ እና ህዝቡ መሰዊያ ሲገነቡ

 

ኤልያስ ሕዝቡ ጉድጓዱን ውሃ እንዲሞሉ እና በመሠዊያው እርጥብ እንጨት ላይ ለሦስት ጊዜ እንዲያፈስሱ ጠየቃቸው። ውሀው እንጨቱን እና መሰዊያውን አረጠበ። ጉድጓዱንም ሁሉ ሞላ። 1ኛ ነገሥት 18፥33–37

 

Description: ኤልያስ በመሰዊያው አጠገብ ሲጸልይ

 

ኤልያስ እውነተኛውን የእግዚአብሔርን ሀይል እንዲያሳይ ወደ ጌታ ጸለየ። የጌታ እሳት ወረደች እናም መስዋዕቱን፣ እንጨቱን፣ ድንጋዮቹን፣ እና ውሀውን በላች። ህዝቡም የኤልያስ አምላክ እውነተኛ እግዚአብሔር እንደሆነ አወቁ። ኤልያስ ድርቁ እንዲያበቃ ጸለየ፣ እናም ጌታ ዝናብን ላከ። 1ኛ ነገሥት 18፡38-41

ይህን አይነት አገልግሎት እኛስ በዘመኛችን ላይ እንዴት ነው? ኃጢአትን አመቻምቸን እያየን እንዳላየን እየሆንን መሆናችን እግዚአብሔርን እንደማያስደስተው እንረዳለን?

7.  መንግስታትን ፈርተው አልኖሩም

በተለይ በዕብራውያን አስራ አንድ ላይ ያለውን የእምነት አባቶችን ታሪክ ወይም መልዕክት በትክክል ለተረዳና ላወቀው፣ ፍርሃት የሚባልን ነገር በሕይወታቸው ላይ አንመለከትም፡፡ ይልቁኑ ሲመሰክርላቸው መንግስታትን ድል ነስተው መኖራቸውን እናያለን፡፡ የእግዚአብሔርንም ስም አስከብረው ማለፋቸውን፣ በዘመናቸውም ላይ በፅድቅ ኖረው ተፅዕኖን ፈጥረው አልፈዋል፡፡

7.1.   ዳዊት- ጎልያድን

ዳዊት በታመነበት እግዚአብሔር ጎልያድን ዋነኛ የፍልስጥኤምን ተዋጊ አዋጊን ገጥሞ እስራኤልን ነፃ አውጥቷል፡፡

7.2.   ሙሴ- ፈርኦንን

ሙሴ በእግዚአብሔር ምሪትና ትዕዛዝ ፈርዖን ፊት በመቅረብ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ነፃ አውጠቷል፡፡

7.3.   ኢዩ- ኤልዛቤልን

ችላ ልትባል የማትገባዋን፣ የእግዝአብሔርን ነቢያት የፈጀችን በምንም መልኩ ኢዩ ሊታገሳት ያልቻለ ቆራጥ አገልጋይ፡፡ ውሾች እንዲበሉአት የተመኘ ጀግና አገልጋይ፣ የዘመኑ ተጽዕኖ ፈጣሪ አገልጋይ፣ ለእግዚአብሔር የጨከነ፣ ተፅዕኖን በማድረግ የእግዚአብሔርን ስም አስከብሯል፡፡

አሜን እኛም እንዲሁ ማድረግ ይሁንልን፡፡

ተባረኩ

ወንድም በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

 

የወንጌል እና የትውልድ ባለ አደራነት

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

እግዚአብሔር በዘመናት ሁሉ የልቡ የጥልቅ ሃሳብ የፈጠረው  የሰው ልጅ ደህንነት ነው። ሰው በተለይ ለነፍሱ ደህንነት፣ መኖር ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን እግዚአብሔር አሳልፎ ሰጥቶአል፣ ወደ ምድርም ክብሩን ትቶ የአባቱን ትዕዛዝ ሊፈፅም መጥቶአል። እግዚአብሔር የፈጠረው የሰው ልጅ እንዲጠፋበት አይፈልግም፣ ይልቁንም የሰውን ልጅ በአድራሻው ያለበት ድረስ መጥቶ በስም ጠርቶ ይፈልገዋል። "አዳም ሆይ ወዴት ነህ" ብሎ መምጣቱ እግዚአብሔር ምን ያህል የፍቅር አምላክ መሆኑን አስረጂ ነው። በተለይ በዚህ አለም፣ በምድር ላይ ያለን አገልጋዮች ለምንመራቸው የእግዚአብሔር ህዝቦች የዚህን ያህል ልብ ከሌለን የወንጌልን እና የትውልድን አደራ እየተወጣን አለመሆኑ ልብ ልንለው የሚገባ አቢይ ጉዳይ ነው። 

በተለይ ከቀደሙት አባቶች በውል ልንማረውና፣ ልንረዳው ይልቁኑ በህይወታችን እና በቤተክርስቲያን ልንተገብረው የሚገባ ጉዳይ ቢሆን እና ቢኖር ለወንጌልና ለትውልድ ያላቸው የፀና አቋም ነው። ከራሳቸው በላይ ለወንጌል እና ለትውልድ ያላቸው የማይናጋ እና የማይናወጥ ሙሉ ሃሳባቸው እና ማንነታቸው፣ ከራሳቸው ጥቅም በላይ ለእግዚአብሔር ህዝብ ያላቸው የፀና እምነት በተለይ ከራስ ምቾት ርቆ ከእግዚአብሔር ህዝብ ጋር መከራ ለመቀበል መወሰኑ የሙሴ ትልቅ አብነትና ምሳሌያችን ነው። 

"ለወንጌል ሁሉን አደርጋለሁ" ማለት በህይወት ላይ ይህን የመሰለ ውሳኔ የለም፣ "የማይጠፋን አክሊልን" ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያሸልም የቆራጥ አገልጋይ አቋም ነው። 

የቀደሙ አባቶች ከእግዚአብሔር የተቀበሉት አደራ በተለይ ለእግዚአብሔር ህግ እና ለትውልድ ያላቸው አደራ በጣም የሚገርም እና ለእግዚአብሔር ጉዳይ ያላቸው የፀና አቋም ዛሬ ላይ ላለን የእግዚአብሔርን መንግስት እያገለገልን ላለን ትልቅ ትምህርትና የራሳችንንም አቋም ልናይበትና ልንፈትሽበት፣ ማስተካከል የሚገባን ነገር ቢኖር እንኳን ትልቅ ትምህርት ሰጥቶን ያልፋል።

የቀደሙት የእምነት አባቶች በእግዚአብሔር፣  በእግዚአብሔር ህዝብና በእግዚአብሔር ህግ (ወንጌል) ላይ ያላቸውን አገልግሎት ስንመለከት፣ ዛሬ በድኀሰረ ስልጣኔ ዘመን ላለን ዘመነኞች አንድ አብይና አንኳር ነገር ጥሎልን ስለሚያልፍ ለትምህርት መመልከቱ ተገቢ ነው።

ባለ አደራነት ምን ማለት ነው?

ባለ አደራነት ማለት ለአንድ የተወሰነ ጉዳይ፣ ክንውን ወይም ግዴታ ለአንድ ግለሰብ ኃላፊነት ወይም ስልጣን መስጠት ማለት ነው። አንድ ግለሰብ አንድን ነገር ለሌላ ሰው ሲሰጥ፣ የተሰጠውን ኃላፊነት በብቃት በታማኝነት እና በኃላፊነት እንዲወጣ በእሱ ላይ እምነት በመጣል እና በመስጠት ጉዳዩን መጣል ነው። 

አደራ መስጠት በበላይነት፣ የውሳኔ ሰጪነት ስልጣን መስጠትን፣ ምስጢራዊ መረጃን መጋራትን ወይም ጠቃሚ ጉዳዮችን መጠበቅና ማቆየትን ሊያካትት ይችላል። 

የአደራ አብይ ጉዳይ በአደራ፣ በመተማመን የተሰጠው ሰው ማንነት ላይ በመተማመን እና በማመን ላይ የተመሠረተ ነው።

ብሉይ ኪዳን

ሙሴ ለኢያሱና ለካሌብ የሰጠው ትዕዛዝ 

እግዚአብሔር አስቀድሞ ሙሴን በኮሬብ ተራራ ተገልጦለት የነገረው ትዕዛዝ በተለይ ሕዝቡ እንዴት እና በምን አይነት መንገድ መሄድ እንዳለባቸው ለሙሴ በግልፅ ሲነግረው በዘዳግም 29:9 በውል እንመለከታለን። ለሕዝቡ ይከናወንላቸው ዘንድ መከናወኛውን እርሱም የቃል ኪዳኑ ቃሎች ይጠበቁ ዘንድ እና ያደረጉም ዘንድ ነገረው። ይህንኑ ትዕዛዝ በኢያሱ 1:7-8 ያለውን ቃል እግዚአብሔር መልሶ ኢያሱን ሙሴ ያዘዘህን በማለት የአደራን መቀበል ያስታውሰዋል። ይህንኑ ቃል በአደራነት ኢያሱም ለእስራኤል ቤት ሲናገር እንመለከታለን።

ኢያሱ የእስራኤል ሽማግሌዎችን

በተለይ ኢያሱ ከሙሴ መሞት በኋላ የእስራኤልን ህዝብ ሊመራ ከሙሴ በአደራ የተቀበለ ተተኪ አገልጋይ ነው። ካሌብም አብሮት የተቀበለ መሆኑ አይዘነጋም። የመከናወንና የስኬት መንገዱ ያለው በእግዚአብሔር ህግ ውስጥ እንደሆነ ሙሴ አበክሮ የነገረው ሲሆን ይህንንም እንዲያስቀጥል እግዚአብሔር ሙሴ የነገረውን ኢያሱን አስታወሰው። ኢያሱ 1:7-8 መመልከት ይቻላል።

ኢያሱም እንዲሁ በሽምግልናው በተለይ በመሞቻው ጊዜ የእስራኤልን ሽማግሌዎች እና ነገዶች በመሰብሰብ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ከእግዚአብሔር እና ሲመራቸው ከነበረው ሙሴ በአደራ የተቀበላቸውን ህዝቦች ስኬት እና መከናወን እንዲሆንላቸው ከእግዚአብሔር ህግ ፈቀቅ እንዳይሉ የእግዚአብሔርን ህግ በአደራ እንደ ተቀበለ በአደራ ሲሰጣቸው በኢያሱ 23:1-6 መመልከት እንችላለን። 

ዳዊት ልጁን ሰለሞንን

ዳዊት ከልጅነት እግዚአብሔር በብዙ የህይወት ጉዳና ውስጥ ያሳለፈው፣ እግዚአብሔር በምድረበዳ በእረኝነት ህይወቱ ብዙ ፈተናዎችን በእግዚአብሔር ሃይልና እርዳታ የኖረ፣ የመሪነትን እና የጦረኝነትን ህይወት፣ የእረኝነትን ህይወት እግዚአብሔር ያሰለጠነው ትልቅ የእግዚአብሔር ልብ ያለው ጀግና ንጉስ ነው። በተለይ በመዝሙር 119 ላይ የፃፋቸው በእግዚአብሔር ህግ ላይ በዚህ በተጠቀሰው መዝሙሩ ላይ እውቀቱን መረዳት እንችላለን። ምን ያህል ሕጉን ይዘን ስንኖር መከናወን እንዳለ ቁልጭ አድር ጎ ያሳየናል። ለዚህ ነው በተለይ የዳዊት የህይወቱ ማብቂያ ላይ ከመሞቱ አስቀድሞ ምን ማድረግ እንዳለበት በእግሩ በተተካው ልጁን ሰለሞንን በብርቱ ሲመክረው የምናየው። 1ኛ ነገሥት 2:3 ላይ ሰለሞን ምን ማድረግ እንደሚገባው የህይወት ዘመን ምክርን ዳዊት አባቱ በአደራ ሲመክረውና አስረግጦ ሲነግረው በዚህ ምዕራፍ ላይ እንመለከታለን። 

በዚህ ትምህርት ምን ያህል ዳዊት ለእግዚአብሔር ህግ እና ለትውልድ አደራነት እንደሚጨነቅ መመልከት እንችላለን። አደራነት ለቀጣይ ለእግዚአብሔር ህግና ለትውልድ ማሰብ መቻል ማለት ነው።

አዲስ ኪዳን

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለጴጥሮስ የሰጠው አደራ

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አባቱ ከመሄዱ አስቀድሞ ለጴጥሮስ የነገረው የአደራ መልዕክት እንደነበረ ሁላችን የማንዘነጋው ብርቱ ጉዳይ ነው። ይህንንም አደራ እንደምስክር የተመለከተው ዮሐንስ በመልዕክቱ በጥንቃቄ ሰድሮ ዛሬ ላይ ላለን አገልጋዮች ፅፎልናል።

 አደራ አደራን በሰጠው በሰጪው ልክ ተረድተን እና ተገንዝበን የምንቀበለው ብርቱ መልዕክት እና ትዕዛዝ ነው። በተለይ በዮሐንስ 21:15-17 ያለው መልእክት ለእኛም በዚህ ዘመን ላለነው አገልጋዮች አደራ ምን ያህል ከባድ የሆነ ኃላፊነትና ተጠያቂነት ያለው አገልግሎት መሆኑን መረዳትና ማወቅ እንዳለብን በአፅንኦት ያሳየናል።

ጌታ ኢዩበዘኑ ሁሉ ምን ያህል ለትውልድ እንደሚጨነቅ ማየት የምንችለው ብርቱ እና ወሳኝ ጉዳይ ነው። ምክንያቱም ለቀጣይነቱ በትውልድ ላይ ምን ያህል መሠራት እንዳለበት አስረግጦ ይነግረናል። "ህፃናት ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ አትከልክሉአቸው" ማለቱ ለትውልድ ምን ያህል አፅንኦት ሰጥቶ እንደሚናገር ማወቅ ይቻላል።

ሐዋርያው ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ 

ጢሞቴዎስ ልጄ ሆይ፥ አስቀድሞ ስለ አንተ እንደ ተነገረው ትንቢት፥ በእርሱ መልካም ጦርነት ትዋጋ ዘንድ ይህችን ትእዛዝ አደራ እሰጥሃለሁ፤ 1ኛ ጢሞቴዎስ 1፥18።

በመጨረሻም፦

ነገር ግን ወንጌልን አደራ ይሰጠን ዘንድ እግዚአብሔር የታመንን ሆነን እንዳገኘን መጠን፥ እንዲሁ እንናገራለን፥ ልባችንን የሚመረምር እግዚአብሔርን እንጂ ሰውን ደስ እንደምናሰኝ አይደለም። 1ኛ ተሰሎንቄ 2፥4።

ጸሎት

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

በምድር ላይ ካሉ ሐይማኖታዊ ነክ ከሆኑ እምነቶች አንዱ ክርስትና ነው። ክርስትና በባህሪው ዋነኛ አድርጎ ከሚንቀሳቀስባቸው አብይ ሚስጥራት መካከል አንዱ ጸሎት ነው። ጸሎት ለክርስቲያኖች የሁልጊዜ የማይቋረጥ ተግባራቸውና ስራቸው ነው። ሳይከውኑት የሚውሉት ወይም የሚያድሩት ጉዳይ አይደለም።

ጸሎት በሚጸልየውና ጸሎትን በሚሰማው በእግዚአብሔር መካከል ያለን ቁርኝት ማሳያ እና ማመልከቻ ነው።

ጸሎት በውስጡ የሚያካትታቸው አቢይ ጉዳዮች፥ ምስጋና፣ ልመና፣ ምልጃ እና በአጠቃላይ እነዚህን አካትቶ አምልኮ ነው። 

ጸሎት የሰው ልጅ የማይችለውን ጉዳይ እግዚአብሔር አንተ ትችላለህ ብሎን ልመናን ማቅረቢያ መንገድ ነው። ያለ ጸሎት ክርስትና አይታሰብም፣ ሊነጣጠልም የሚችል ጉዳይ አይደለም። 

ጸሎት ከሚደረግባቸው አይነቶች መካከል፦

1- በግል ሊቀርብ የሚችል፦ በተናጠል

2- በቡድን የሚቀርብ፦ በማህበር

3- በባለትዳሮች የሚቀርብ፦ የራሳቸውን ጊዜና ቦታ በመውሰድ

4- እንደ ሃገር የሚቀርብ፦ ለድንገተኛ ጥሪ ሲሆን (እግዚዮታ)

5- በቤተክርስቲያን፦ ለአማኞች የአንድነት ጊዜ ሲኖር የሚደረጉ የጸሎት አይነቶች ናቸው።

በተለይ ክርስቲያን የጸሎት ምንነትን እና እንዴትነት የጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ልንማር የግድ ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአርባ ቀናት ያህል ባለማቋረጥ ጸልዮአል። ለጸሎትም ይተጋ ነበር። የሉቃስ ወንጌል 22:39-49 (መከራው፣ ጽዋው እንዲያልፍ ጸለየ)

ጸሎት የልባችንን መሻት የምንለምንበት ዋነኛ መንገድ ነው። መዝሙረ ዳዊት 37:4

ምኞታችንን ከበረከቱ እንዲያጠግበን የምንለምንበት ነው። መዝሙረ ዳዊት 103:5

1- ጸሎት ልናበዛው የሚገባን ነው፦ ምናሳንሰው አይደለም

የምንፈልገውን ከእግዚአብሔር እስከምናገኝ ድረስ የምንከውነው ሥራ ነው፣ የምንፈልገውን እስከምናገኝ  አብዝተን ልናደርገው የሚገባ ነው።

ጸሎትዋንም በእግዚአብሔር ፊት ባበዛች ጊዜ ዔሊ አፏን ይመለከት ነበር። 1ኛ ሳሙኤል 1:12

2- በልብ የምንናገረው ነው፦ ሚስጢር ነው

ድብቅ የሆነን ለእግዚአብሔር ብቻ የምንነግረው ነው። ማንም ሊሰማው የማይገባ ነገራችንን የምንገልጽበት ነው። ሐናም በልብዋ ትናገር ነበር፤ ድምፅዋም ሳይሰማ ከንፈርዋን ታንቀሳቅስ ነበር፤ ኤሊም እንደ ሰከረች ቆጠራት። 1ኛ ሳሙኤል 1:13

3- የምንጮኸው ነው፦ ጉዳያችንን አበክረንና አጽንኦት ሰጥተን የምናቀርበው ነው

ወደ እግዚአብሔር የምንጮኸው፣ እግዚአብሔርም የሚመልስበት አቀራረብ ነው። ክርስቲያን አንዳች የሚደንቅን ነገር የሚፈልግ ነው። ለዚህም ነው እግዚአብሔር እንደ ትዕዛዝ የሚነግረን። "ወደ እኔ ጩኽ፥ እኔም እመልስልሃለሁ፤ አንተም የማታውቀውን ታላቅና ሃይለኛ ነገርን አሳይሃለሁ። ትንቢተ ኤርምያስ 33:3

4- ጸሎት በትጋት ይደረጋል

ጸሎት አንዴ ሲመቸን፣ አንዴ ሳይመቸን የምናደርገው አይደለም። በምቾትም ይሁን በማይመች ሁኔታና ጊዜ የምናደርገው አይደለም። የእኛን ያለመድከም ይፈልጋል።

ጸሎት በብርታት ጊዜ የምንተወው፣ በድካም ጊዜ የምንቀጥለው አይደለም። ከሁኔታ ያለፈ ነው። በሁኔታም የሚወሰን፣ ወይም የሁኔታ ጥገኛ አይደለም። በምንም ሁኔታ እንሁን የምንተወው አይደለም። ስለዚህ፦ "ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ፤ መንፈስስ ተዘጋጅታለች ሥጋ ግን ደካማ ነው አለው። ማቴዎስ 26:41።

ወደ ደቀመዛሙርት መጣ፤ ተኝተውም አገኛቸውና ጴጥሮስን፦ እንዲሁም ከእኔ ጋር አንዲት ሰዓት እንኳ ልትተጉ አልቻላችሁምን? ማቴዎስ 26:40

5- ጸሎት ያለማቋረጥ የሚደረግ ነው

አንድ ወቅት ጸልየን በሌላ ቀን የምንተወው አይደለም፣ ጸሎት የሁልጊዜ ሥራችን ነው፣ ከእግዚአብሔር ጋር የምንነጋገርበት ነው። ስለዚህ ልናቋርጠው የሚገባን አይደለም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር በኖረበት ጊዜ ከከወናቸው ድርጊቶች አንዱ ባለማቋረጥ መጸለዩ ነው። ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚለን፦ ሳታቋቂጸልዩ፤ በሁሉ አመስግኑ፤ ይህ የእግዚአብሔር ፈቃድ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ እናንተ ነውና። 1ኛ ተሰሎንቄ 5:17-18።

የቀደሙ አባቶችና ጸሎት

የቀደሙ አባቶች ከጸሎት ጋር የጠነከረ ቁርኝት አላቸው። ጸሎት እጅግ በእነርሱ ህይወት ውስጥ የተጣበቀ ነው። በጸሎት አይደራደሩም፣ ወደ ኋላም አይሉም፣ ጸሎት ልማዳቸው ነው። በምንም አይነት ሁኔታ ውስጥ ይገኙ ጸሎትን አያቋርጡም።

1- አብርሃም፦ የእምነት አባት

በአብርሃም ሚስት በሣራ ምክንያት በአቢሜሌክ ቤት ማህፀኖችን ሁሉ ዘግቶ ነበርና አብርሃም ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ሁሉም ተፈወሱ ወለዱም።  ዘፍጥረት 20:17-18

2-ይስሐቅ፦ ለአባቱ አብርሃም የታዘዘ

ስለ ሚስቱ መካንነት ጸለየ፣ እርሷም ፀነሰች። መካንነቷ ቀረ፣ ተወገደ፣ ዘር ተተካ። ዘፍጥረት 25:21

3- ሙሴ፦ ቁጣ እንዲመለስ ጸለየ

እግዚአብሔር በሕዝቡ ኃጢአት ምክንያት በመቆጣቱ፣ ቁጣው በመንደዱ ምክንያት እግዚአብሔር ከቁጣው  እንዲመለስ እግዚአብሔርን ይለምን ይጸልይ ነበር። ዘጸአት 8:30፤ ዘኁልቁ 11:2፤ 21:8።

4- ሃና፦ የስለት ጸሎት

ሃና በማህፀኗ መዘጋት፣ በመሃንነት የተነሳ በጣውንቷ ማስቆጣት ተበሳጭታ ወደ እግዚአብሔር የስለት አዘል ጸሎት ጸለየች፣ እግዚአብሔርም ሰማት፣ ልጅም አገኘች በስለቷም መሠረት ለእግዚአብሔር መልሳ ሰጠች። ስለት አዘል ጸሎት አቀረበች። 1ኛ ሳሙኤል 1:10፤ 1:12-14።

5- ኤልሳዕ- ሙት ህፃን በእጁ ተፈወሰ

ኤልሳዕ ሁሉን ወደሚችል ወደ እግዚአብሔር ጸለየ የሞተውም ህፃን በእጁ እግዚአብሔር አስነሳው። 2ኛ ነገሥት 4:30-34፤ 6:18።

ስለዚህ ጸሎት ከእኛ ከክርስቲያኖች ተነጥሎ፣ ተለይቶ የሚታይና የሚገኝ አይደለም። ጸሎት ለክርስቲያኖች ወሳኝ ጉዳይ ነው።

ስለዚህ የጸሎት ጊዜና ቦታ በተለይም የጸሎት መሰዊያ ሊኖረን ይገባል። የጸሎት ጊዜና ቦታ ይኑረን፣ የጸሎት መሠዊያን እናበጅለት። 

የቀደሙት የእምነት አባቶች ከሚለዩባቸው ባህሪያት አንደኛው መለያ ባህሪያቸው በጸሎት ማመንና የጸሎት ስፍራ ማበጀትና ማዘጋጀታቸው ነው።

ከፊታችን ትልልቅ ፈተናዎች ይመጣሉ ይህንንም የምናልፈው በጸሎት ብቻ ነው። እግዚአብሔርን በማነጋገር። 

ጸሎት በእግዚአብሔር ፊት ሆነን እጅግ ትንሽ ጊዜን በመውሰድ የምንለምንበት፣ እጅግ ብዙ ከእግዚአብሔር የምንሰማበት ነው።

በመጨረሻም፦ "... የጻድቅ ሰው ጸሎት በሥራዋ እጅግ ኃይል ታደርጋለች።" ያዕቆብ 5:16

ስለዚህ ቅዱስ ሁሉ በምቹ ጊዜ ወደ አንተ ይለምናል፤ ብዙ የጥፋት ውኃም ወደ እርሱ አይቀርብም። መዝሙር 32:6።

አቤቱ፥ በመልካሙ ጊዜ ጸሎቴ ወደ አንተ ነው፤ አቤቱ በምህረትህ ብዛት በማዳንህም እውነት አድምጠኝ። መዝሙር 69:13

ለምኑ፥ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፥ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፥ ይከፈትላችሁማል። ማቴዎስ 7:7።

ተባረኩ

አገልጋይ በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

ፍጹምነትን መያዝ (INTEGRITY, JUSTIFICATION, PERFECTION)

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ

ክርስትና በእግዚአብሔር ፊት በምመካድ፦ለሰው ህይወትና መስተጋብር የምንገልጸው ሕይወት ነው። እግዚአብሔር የሚጠላውን ጠልተን፣ እግዚአብሔር የሚወደውን ወድደን እግዚአብሔርን እያስደሰትን የምንኖረው ሕይወትና ተግባራዊ እንቅስቃሴ ነው። 

Read more: ፍጹምነትን መያዝ (INTEGRITY,...

Subcategories

ነገረ ድነት/ Salvation

  • የተቃኘንበትን ቅኝት ያጠፉ ቅኝቶች
  • እረኝነት እና መጋቢነት
  • የታጠቀ ትውልድ
  • የትውልድ አደራ
  • እስክንድሮሶች

Article Categories

  • Literature/ስነ-ጽሑፍ
  • Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ
  • The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ
  • Testimony/ምስክርነት
  • Religious News/ሐይማኖታዊ ዜና
  • Churches/ቤተ ክርስቲያን

Login Form

  • Forgot your password?
  • Forgot your username?
Copyright © 2026 yegizewkal. All Rights Reserved.