yegizewkal
ቃልህ ተገኝቶአል እኔም በልቼዋለሁ አቤቱ፥ የሠራዊት አምላክ ሆይ፥ በስምህ ተጠርቻለሁና ቃልህ ሐሤትና የልብ ደስታ ሆነኝ። ትንቢተ ኤርምያስ 15፥16

  • Home/መነሻ ገጽ
  • Gospel Thoughts/የወንጌል አስተምህሮ
    • ነገረ ድነት/Salvation
  • The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ
    • Literature/ስነ-ጽሑፍ
    • ከመጽሐፍት ዓለም
  • Churches/ቤተ ክርስቲያን
    • Religious News/ሐይማኖታዊ ዜና
  • Testimony/ምስክርነት
  • ማስታወቂያ/Advertisement
  1. You are here:  
  2. Home
  3. The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ

The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ

በመከራ ውስጥ የሚፀና ማንነት

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ

በመከራ ውስጥ የሚፀና ማንነት

“በእኔ ሳላችሁ ሰላም እንዲሆንላችሁ ይህን ተናግሬአችኋለሁ። በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ።” — ዮሐንስ 16፥33።

በአለም ስላለን ብቻ እኛ ክርስቲያኖች መከራ ይደርስብናል ማለቱ ተላላነት ነው፣ በአለም መኖሩ ሳይሆን ክርስቲያን መከራ የመጣበት በአለም ሳለን በእውነት በክርስቶስ ስላለን ነው። በእርግጥ የክርስቶስ ተከታይ ክርስቲያን መባሉ እንዳለ መከራ ቢያመጣም በእርሱ ካለን፣ እንደ ቃሉ ፈቃድ ስንኖር፣ የቃሉን ፈቃድ ስንፈፅም፣ ቃሉን ስንተገብር፣ የኃጢአትን መንገድ ጠልተን በክርስቶስ መንገድ መሄድ በእነዚህ ምክንያት እጅግ የበዛ መከራ መድረሱ አይቀሬ ነው።

በእርግጥ መከራ ፅናትን፣ ትዕግስትን፣ አቋምን የሚፈታተን ቢሆንም በፈተና ውስጥ መፅናቱ የመጨረሻ ዋጋው እጅግ የከበረ ነው። መከራ  በዋናነት ከቆምንበት አቋም መጣል አሊያም ማስጣል፣ ከእግዚአብሔርም ጋር የነበረንን ብርቱ ቁርኝትና ግንኙነት ማበላሸት አሊያም ማቋረጥ ነው።

በተለይ የከበረ የእግዚአብሔር እቅድና አላማ ያለበት የሰይጣን ኢላማ የሆነ ሲሆን ይህንን ብርቱ ጉዳይ አለም፣ ሰይጣን እና ስጋውያን ኢላማ አድርገውት መከራን እና ጫናን በማብዛት ሊያስጥሉት ይተጋሉ። መከራ በባህሪው ግፊቱ ከጨለማው አለም ገዢ በሚመጣ ጫና የሚከሰት ሲሆን የመጀመሪያ አላማ አድርጎ የሚነሳው በእግዚአብሔር ፈቃድ የሚኖርን፣ በእግዚአብሔር ህግ፣ትዕዛዝ፣ ሥርዓት የሚሄደውን በማስጨነቅ በእርሱ ላይ ያለውን በማስጣል ሙሉ በሙሉ ከእግዚአብሔር ነገር መነጠል ነው። 

1- የቀድሞው መከራ

ቀድሞ የነበረው የመከራው አይነት ፊት ለፊት በአካላዊ ጥቃት መከራ መድረስ ሲሆን ይህንንም መከራ የተወጡት በእግዚአብሔር ላይ ባላቸው ጽናት እና አቋም መከራውንና የመከራውን ዘመን ተሻግረውታል።

በተለይ የመከራውን ዘመን የተሻገሩት አንድ ባዩትና በተረዱት እና  በገባቸው ብርቱ ጉዳይ ያን ያዩትን ላለማጣት የመከራን ዘመን ድል አድርገው አልፈዋል። በተለይ በሰማይ ከመከራ ድል በኋላ የሚያገኙት እና የሚጠብቃቸውን ሽልማት፣ በሰማይ ሃገር እንዳለ፣ ሥፍራ እንደተዘጋጀላቸው ጠንቅቀው በማወቃቸው የመከራው አይነት እና መብዛት ከሚያገኙት ዘላለማዊ ነገር ጋር ሊወዳደርና ሊነፃፀር እንደማይችል በማወቅ እንደ ተራ፣ ጉድፍ እና ከንቱ፣ ረብ የሌለው እንደሆነ በማወቅ ንቀው፣ ጠልተው ኖረዋል። “እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፥ ጽድቅን አደረጉ፥ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፥” — ዕብራውያን 11፥33። “አሁን ግን የሚበልጠውን እርሱም ሰማያዊ አገር ይናፍቃሉ። ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካቸው ተብሎ ሊጠራ በእነርሱ አያፍርም፥ ከተማን አዘጋጅቶላቸዋልና።” — ዕብራውያን 11፥16።

መከራ እንዳለ አምኖ መቀበል

በተለይ ጳውሎስ አንድ የገባው፣ ሌሎችንም ሰዎች በገባው መንገድ አብሮ በመጋራት ከእርሱ ጋር እንዲቀጥሉ ይነግር ነበር። "አብረኸኝ መከራ ተቀበል"። አንድ የገባው ነገር ያለው ጳውሎስ በክርስትና እና በክርስቶስ መኖር ምንኛ ዋጋ እንደሚያስከፍል፣ መከራ ተነጥሎት እንደማይታይ በዋናነት ገብቶታል። ለዚህም ነው ለመንፈሳዊ ልጁአንድ ብርቱ ነገር ያንንም አምኖ እንዲቀበል ያህል የሚነግረው። “እንግዲህ በጌታችን ምስክርነት ወይም በእስረኛው በእኔ አትፈር፥ ነገር ግን እንደ እግዚአብሔር ኃይል መጠን ስለ ወንጌል አብረኸኝ መከራን ተቀበል፤” — 2ኛ ጢሞቴዎስ 1፥8። “እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ በጎ ወታደር ሆነህ፥ አብረኸኝ መከራ ተቀበል።”   — 2ኛ ጢሞቴዎስ 2፥3።

ለመከራ ራስን ማዘጋጀት

የጳውሎስን ህይወት ስንመለከት ለክርስቶስ እና ለወንጌል ራሱን ማዘጋጀቱ ምን ያህል እንዳመነበት መገለጫ ሲሆን ለዚህም እራሱን በማሳመን ለመጋደል እና መጋደሉ ምን ያህል እንደ ሚያደክመውም ጠንቅቆ ያውቃል። ይህም ብቻ አይደለም ለመንፈሳዊ ልጁ ለጢሞቴዎስም ይህንን የተረዳውን መጋደል እንዳለበት ይነግረዋል። “ለዚህም ነገር ደግሞ፥ በእኔ በኃይል እንደሚሠራ እንደ አሠራሩ እየተጋደልሁ፥ እደክማለሁ።” — ቆላስይስ 1፥29። “መልካሙን የእምነት ገድል ተጋደል፥ የተጠራህለትንም በብዙም ምስክሮች ፊት በመልካም መታመን የታመንህለትን የዘላለምን ሕይወት ያዝ።”   — 1ኛ ጢሞቴዎስ 6፥12።

2- ዘመነኛው መከራ

ዘመነኛው መከራ ብዙውን ጊዜ ከቁብ የማናስገባው ግን በእጅጉ የክርስትና ህይወታችንን እየሸረሸረ ያለ ዝምተኛ፣ ለዘብተኛ መከራ ግን ያላስተዋልነው የመከራ አይነት ነው። ይህ መከራ እጅግ ወረራ ያለበት እያስደሰተን ነገራችንን የሚነጥቅ፣ ወሳኝ ለሆነ ጉዳይ ጊዜ እንዳይኖረን የሚያደርግ የሚያዘናጋ መከራ ነው። ብዙውን ጊዜ የምንነቃው የክርስትና ህይወታችንና አገልግሎታችን እንደቀድሞው አልሆን ሲለን ነው። መች እንደጎዳን አንነቃም።

ዘመናዊ ወይም ዘመነኛ የክርስትና ፈተና እና መከራ በዛሬው ዘመን ክርስቲያኖች የሚያጋጥሟቸውን መንፈሳዊ፣ ማህበራዊ፣ እና ሥነ-ምግባር  በእጅጉ የሚያጠቃና መንፈሳዊ እሴቶቻችንን እየጎዳው ነው። ። እነዚህ ፈተናዎች ከጥንት ዘመን በተለየ መልኩ ይታያሉ፣ ግን መሠረታቸው እምነትን ማፍረስ እና ከእግዚአብሔር በእጅጉ ማራቅ ነው።

በተለይ የሚጎዱብን እና የሚጠቁብን መንፈሳዊ አብይ እሴቶቻችን፦

  1. የእምነት መደከም (Spiritual Weakness)- ዛሬ ብዙ ሰዎች ከመንፈሳዊ ሕይወት ተለይተው ወደ ዓለማዊ ነገሮች በመሄድ እምነታቸው ይደክማል። በተለይ በአለማዊ እሳቤዎች በመሳብ መንፈሳዊ እሴቶችን በእጅጉ ሲጎዳ ዋነኛ ጉዳዮቻችን፦ መጽሐፍ ቅዱስ የማንበብጊዜ፣ ጸሎት ጊዜ እና የህብረትና የአንድነት ጊዜ እየቀነሰ ነው። አብዛኛው ክርስቲያን የዚህ ነገር ተጠቂ ከመሆኑ የተነሳ የበረታ በመጥፋቱ የደከመውን የሚያበረታ አለመኖሩ በዘመነኞቹ ዘንድ ክርስትና ከብዶ አይታይም። ከታየም የወረት፣ የመርሃ ግብር ጉዳይ ካልሆነ በቀር የክርስትና መንፈሳዊነት በቅጡ በክብር ሲገለጥና ሲታጀብ ባለመታየቱ ከበሬታን የመነፈግ ያህል እየሆነ መጥቷል።
  2. የዓለም ፍላጎት (Worldliness)- ያልተጎሰመ ስጋ ፍላጎቱ ባለመገደቡ ቁጥጥር ያልተደረገበት የሀብት ፍላጎት፣ ዝና፣ ቅጥ ያጣ የደስታ ፍላጎት እምነትን ይነካል። ያለኝ ይበቃኛልን የማይፈልግ፣ እግዚአብሔርን መምሰልን እጅግ ማትረፊያ እንደሆነ የማይረዳና የማይገነዘብ፣ በመጠን መኖር መርሁ ያልሆነ፣ ክርስቲያኖች ከመንፈሳዊ እሴቶች ይልቅ ዓለማዊ ነገሮችን ሲያስቀድሙ ይታያሉ። በአለም ያለውን መውደድ ምንም ረብ እንደሌለው አለማወቅ አንዱ መከራና ፈተና መሆኑን አለመረዳት የክርስቲያን ፈተና መሆኑን አለማወቅ እየጎዳ ይገኛል። ብዙዎች በዚህ እሳቤ በመጠመድ እና በመተብተብ ስተዋል፣ ከእግዚአብሔርም መንግስት ርቀዋል።
  3. የሥነ-ምግባር መቀነስ (Moral Decline)- ዛሬ ዓለም ውስጥ የሚታዩ የሥነ-ምግባር መጥፋት ከእግዚአብሔር ሕግ በመራቅ የሚመጣ፣ የእግዚአብሔርን ህግ ቀንና ለሊት አለማሰላሰል ከማሚያመጣው አንደኛው ለዘብተኛ መከራና ፈተና ሆኖ የማናስተውለው ግን ከመድከምና ከመውደቅ በኋላ የምንነቃበት አይነት ነው። በዚህ ዘመን ክርስቲያኖች ከሚታሙበት፣ በሌሎች አለማውያን ዘንድ እንዲህ ከይነት አይተን አናውቅም እስከሚባል ድረስ ያደረሰ እጅግ ክፉ ጉዳይ ነው። (ሐሰት፣ ዝሙት፣ ስርቆት) እንኳን በክርስቲያኖች መካከል እየተገኙ ናቸው። 
  4. የሐሰት ትምህርት (False Teachings)- የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት የሚያዛብ ሐሰተኛ ትምህርቶች በብዙ ቦታ ተስፋፍተዋል። ይህም የግል የክርስትና እምነትን እየጎዳ ያለ ነው። የእውቀት ማነስና በእግዚአብሔር ቃል እውነት ላይ ባለመደገፍ፣ ግን ሌሎች በማጣመም በሚገልጡት ከእውነት አፈንግጥ በመሳብ ብዙዎች ስተዋል። ብዙውን ጊዜ የሐሰት ትምህርት ከውጭ ባሉት ዘንድ ብቻ የሚገኝ አድርገን እንጠብቃለን፣ ይህ ስህተት ነ፣ በቅርብ ያለም እንደሚስት እና ሐሰትን እንደሚዘራ ማወቅ አለብን። ብዙውን ጊዜ ለራሳቸው እና ለትምህርታቸው የማይጠነቀቁ የበዙበት ዘመን ይህ ያለንበት እንደሆነ ብዙዎቻችን አንረዳም። ከእውቀት መብዛት አጉል የሚራቀቁና ባልተማሩት ዘንድ እጅግ የተወሳሰበና የተራቀቀ አስተምሮቶች መብዛት፣ ብዙዎች በመምታታ መገኘታቸው በአቋማቸው ላይ እና በእምነታቸው ላይ እርግጠኝነትን በማጣት፣ በምትኩ ጥርጥርን በማጫር እርግጠኝነት በመተው ሸሽተዋል። ከማን መማር እንዳለባቸው እስከመጠራጠር ተደርሷል። ለራሳቸውና ለትምህርታቸው የማይጠነቀቁ የበዙበት ዘመን ነው፣ ይህም አንደኛው መከራ መሆኑንም አለመረዳት ድካም ነው።
  5. ቴክኖሎጂ እና ማህበራዊ ሚዲያ ማህበራዊ ሚዲያ (Technology and Social Media)- አንዳንድ ጊዜ ጥሩ ቢሆንም፣ አስተሳሰብን የሚያስቀይር፣ ጊዜን የሚያጠፋ እና ከእግዚአብሔር የሚያርቅ ሊሆን የሚችል ሲሆን በተለይ ጊዜያችንን በእጅጉ በማዘናጋት የሚሰርቁብንና እጅግ ድካምን በመርጨት ለእግዚአብሔር ጊዜ እንዳንሰጥ፣ በዋናነት የክርስትና እሴቶቻችንን በእጅጉ እየጎዳ ያለ የዘመኑ መከራ፣ ፈተና ነው። በዋናነት በእድሜ ደረጃ ያየነው እንደሆነ በጉብዝና የእድሜ ክልል ያለ የዚህ ነገር ተጠቂ፣ እስረኛ-ምርኮኛ ነው።
  6. መከራና አስጨናቂ ሁኔታዎች- በተለይ አለም፣ የጨለማው ገዢ በዋናነት እየሠራበት ያለ ነገር ቢኖር በአለም የምጣኔ ሐብት አለመረጋጋት ላይ እየሠራው ያለው ነገር በአለም ላይ ላሉ መንግሥታት የእራስ ምታት ቢሆንም በተለይ ክርስቲያኖችም የዚህ ነገር ተጠቂ ቢሆኑም የኢኮኖሚ ችግር በዋናነት በአማራጭ መንገድ መምጣቱ ክርስቲያኖች በማይመች መንገድ መምጣቱና ባለመምረጡ የዚህ መከራ ተጠቂ ይሆናል። በጨለማውን አለም ዘዴ (system) አለመቀበል ለከፋ ድህነት፣ ስራ አጥነት በዳረጉ ለሌላ ለከፋ ችግር መዳረጉ አይቀሬ ነው። ስለዚህ የሚያስጨንቅ ዘመን እንደሚመጣ ከወዲሁ ማወቁ ተገቢ ነው።
  7. የአንድነት የህብረት እጥረት የህብረት መጥፋት- በህብረት ውስጥ የሚገኝን የታዘዘ በረከት እንዳናገኝ ካደረጉን ዋነኛው እውነተኛ ህብረት መጥፋቱ ነው። ቢኖር እንኳን ህብረት ለማድረግ የውስጥ ፈቃደኝነት ማነስ ለመከራ ዳርጎናል፣ ይህም አንድ መከራ መሆኑን አለመረዳት የውድቀታችን ሰበብ እና ምክንያት ነው። በተለይ በሰላም ማሰሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ያለን አነስተኛ አመለካከት ለከፋ ግጭት እና ክፍፍል ምክንያት ሆኖአል። ሆኖም ብቻ ሳይሆን መለያየትን እና መከፋፈልን ለሚመኘው ትልቁ መግቢያ ነው። በክርስቲያኖች መካከል ክፍፍል፣ ግጭት እና የአንድነት እጥረት ታላቅ ፈተና ነው። በተለይ መጋመድ አለመቻላችን ጎድቶናል። ብዙዎች መለየትን የሚወዱ ምኞታቸውን የሚከተሉ ናቸው።

መፍትሄ እና መንገዶች

  1. በጸሎት መትጋትና መጽናት፦ “ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ፤ መንፈስስ ተዘጋጅታለች ሥጋ ግን ደካማ ነው አለው።”   — ማቴዎስ 26፥41።
  2. መጽሐፍ ቅዱስን መማርና መከታተል፦ “በወገኑም የእስክንድርያ  ሰው የሆነ ነገር አዋቂ የነበረ አጵሎስ የሚሉት አንድ አይሁዳዊ ሰው ወደ ኤፌሶን ወረደ፤ እርሱም በመጻሕፍት እውቀት የበረታ ነበረ።” — ሐዋርያት 18፥24።
  3. በመንፈሳዊ አንድነት መኖር፦ “በሰላም ማሰሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ።” — ኤፌሶን 4፥3።
  4. ከዓለማዊ ፍላጎት መራቅ፦ “ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል፤” — ቲቶ 2፥12-13።
  5. እውነተኛ ትምህርትን ማሰላሰል፦ “በሐዋርያትም ትምህርትና በኅብረት እንጀራውንም በመቍረስ በየጸሎቱም ይተጉ ነበር።”   — ሐዋርያት 2፥42። “እንደ ክርስቶስ ትምህርት ሳይሆን፥ እንደ ሰው ወግና እንደ ዓለማዊ እንደ መጀመሪያ ትምህርት ባለ በፍልስፍና በከንቱም መታለል ማንም እንዳይማርካችሁ ተጠበቁ።”   — ቆላስይስ 2፥8። “ለሚወጣ ሁሉ በክርስቶስም ትምህርት ለማይኖር ሰው አምላክ የለውም፤ በክርስቶስ ትምህርት ለሚኖር አብና ወልድ አሉት።” — 2ኛ ዮሐንስ 1፥9። በመጨረሻም ዘመናዊ ፈተናዎች ከብዙ አቅጣጫ ቢመጡም፣ ክርስቲያኖች በእምነት በመጽናት እና በእግዚአብሔር ቃል ላይ በመቆየት ማሸነፍ ይችላሉ። በተሸነፈ አለም ላይ እንዳለን ማወቅ አለብን። ዮሐንስ 16፡33።

አገልጋይ በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

+251902910126

በሚበልጥ ክብር መገለጥ

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ

በሚበልጥ ክብር መገለጥ

በዘመናችን እየታየ ያለው እንቅስቃሴ በተለይ ከእግዚአብሔር ቃል አኳያ የምናያቸው አብዛኞቹ ነገሮች አሳዛኝ፣ ልብ ሰባ፣ አስከፊ እና ፀያፍ ናቸው። ክርስቲያን እንደ ክርሰቲያንነት የሚታይበት የሌለው፣ እግዚአብሔርን እከተላለሁ የሚል እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የማይሄድ የበዛበት ዘመን፣ ከተግባራዊ ክርስትና ይልቅ አፋዊ ክርስቲያን እና ክርስትና እያየን ያለንበት ዘመን፣ ለአብነት ምስክር መሆን የማንችል፣ ለሌሎች ለሚያምኑም ይሁን ለማያምኑ መልካም ምስክርነት የሌለን ተላላዎች ሆነን እየታየን ነው። ይህ ማንነት ግን ጨርሶ እግዚአብሔራዊ እና ክርስቶሳዊ እና ክርስቲያናዊ አይደለም። ከጥንት የነበሩ በመጽሐፍ ቅዱስ ያየናቸው የእግዚአብሔር ሰዎች በዚህ ማንነት ተገልጠው አናያም፣ ይልቁኑ መንግስታትን በጽድቅ ኖረው፣ አገልግለው ድል ነስተው እግዚአብሔርን አስከብረው አልፈዋል። በምንም አይነት ሁኔታ ውስጥ ይሁኑ በእግዚአብሔር ነገር እና ጉዳይ አይደራደሩም፣ እስከመጨረሻው በእግዚአብሔር ጉዳይ ይጋፈጣሉ፣ ይወራረዳሉ በመጨረሻም በእግዚአብሔር ያሸንፋሉ። በሚበልጥ ክብር፣ በሚበልጥ በእግዚአብሔር ኃይልና ክብር መገለጥ በዘመኑ ላይ ባለው ክፋት፣ አመፅ፣ ከእግዚአብሔር በተቃራኒ በቆመ ላይ አይሎ፣ ረግጦ፣ አሸንፎና አጥፍቶ በበላይነት በመቆም የእግዚአብሔርን ስም እንዲገን በማድረግ በገዢነት ለመቆየት ወሳኙ ነው። በተለይ የቀደሙት የእምነት አባቶች በምርኮ ዘመን ላይ ተላልፈው ለጠላት በተሰጡበት ዘመን በምርኮ ሐገር የገዛቸውን አሸንፈው የኖሩት በእግዚአብሔር ላይ ባላቸው እምነት፣ በዘመናቸው እየገዛቸውና ልግዛቸው ያለውን አሸንፈው፣ ረትተው የተገኙ በላያቸው ባለው በተገለጠው በእግዚአብሔር ክብር ነው። እግዚአብሔርን አሳይተው፣ አስከብረው፣ በእውነትም የእነርሱ አምላክ በእርግጥም አምላክ ነው አሰኝተው የኖሩት በላያቸው ባለው የእግዚአብሔር ክብር፣ በኖሩለት እግዚአብሔር በምርኮ ሀገር አሸንፈዋል፣ ይህም በተወራረዱበት በእግዚአብሔር ኃይል ነው። በዘመናቸው ላይ ተጽዕኖ ፈጥረው፣ አሳድረው በዘመናቸው ላይ በበላይነት በአሸናፊነት ኖረዋል።

በበብሉይ ኪዳን የነበረው የእግዚአብሔር ክብር ሲገለጥ 

1- ሙሴና አሮን

የአስማተኞችን በትር፦ “እግዚአብሔርም ሙሴንና አሮንን እንዲህ ሲል ተናገራቸው፦”   — ዘጸአት 7፥8። “ፈርዖን፦ ተአምራትን አሳዩኝ ሲላችሁ፥ አሮንን፦ በትርህን ወስደህ እባብ እንድትሆን በፈርዖን ፊት ጣላት በለው።” — ዘጸአት 7፥9። “ሙሴና አሮንም ወደ ፈርዖን ገቡ፥ እግዚአብሔርም እንዳዘዛቸው እንዲሁ አደረጉ፤ አሮንም በትሩን በፈርዖንና በባሮቹ ፊት ጣለ፥ እባብም ሆነች።” — ዘጸአት 7፥10። “እያንዳንዳቸውም በትራቸውን ጣሉ፥ እባቦችም ሆኑ፤ የአሮን በትር ግን በትራቸውን ዋጠች።” — ዘጸአት 7፥12።

2- ኤሊያስ

“ኤልያስም፦ እስራኤልን የምትገለባብጡ፥ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ትታችሁ በኣሊምን የተከተላችሁ፥ አንተና የአባትህ ቤት ናችሁ እንጂ እኔ አይደለሁም።”— 1ኛ ነገሥት 18፥18። “አሁንም ልከህ እስራኤልን ሁሉ፥ በኤልዛቤልም ማዕድ የሚበሉትን አራት መቶ አምሳ የበኣልን ነቢያት፥ አራት መቶም የማምለኪያ ዐፀድን ነቢያት ወደ እኔ ወደ ቀርሜሎስ ተራራ ሰብስብ አለ።”   — 1ኛ ነገሥት 18፥19። “የእግዚአብሔርም እሳት ወደቀች፥ የሚቃጠለውን መሥዋዕቱንም እንጨቱንም ድንጋዮቹንም አፈሩንም በላች፥ በጕድጓዱም ውስጥ ያለውን ውኃ ላሰች።” — 1ኛ ነገሥት 18፥38። “ኤልያስም፦ ከበኣል ነቢያት አንድ ሰው እንዳያመልጥ ያዙ አላቸው። ያዙአቸውም ኤልያስም ወደ ቂሶን ወንዝ ወስዶ በዚያ አሳረዳቸው።”   — 1ኛ ነገሥት 18፥40። “አክዓብም ሊበላና ሊጠጣ ወጣ፤ ኤልያስም ወደ ቀርሜሎስ አናት ወጣ፤ ፊቱንም በጕልበቱ መካከል አድርጎ በግምባሩ ተደፋ።”   — 1ኛ ነገሥት 18፥42።

በአዲስ ኪዳን የነበረው የእግዚአብሔር ክብር ሲገለጥ

  1. ኢየሱስ ክርስቶስ:-  ተአምራቱ: ፈውስ፣ ሙታንን ማንሳት፣ ተፈጥሯዊ ነገሮችን መቆጣጠር ጥቅስ: “ኢየሱስም በከተሞችና በመንደሮች ሁሉ ይዞር ነበር… ሕመምና ድካም ሁሉ ይፈውስ ነበር።” “ኢየሱስም በምኩራቦቻቸው እያስተማረ የመንግሥትንም ወንጌል እየሰበከ በሕዝብም ያለውን ደዌና ሕማም ሁሉ እየፈወሰ በገሊላ ሁሉ ይዞር ነበር።”— ማቴዎስ 4፥23። “ዝናውም ወደ ሶርያ ሁሉ ወጣ፤ በልዩ ልዩ ደዌና ሥቃይም ተይዘው የታመሙትን ሁሉ አጋንንትም ያደሩባቸውን በጨረቃም የሚነሣባቸውን ሽባዎችንም ወደ እርሱ አመጡ፥ ፈወሳቸውም።”   — ማቴዎስ 4፥24። “ከገሊላም ከአሥሩ ከተማም ከኢየሩሳሌምም ከይሁዳም ከዮርዳኖስም ማዶ ብዙ ሕዝብ ተከተሉት።” — ማቴዎስ 4፥25። “ዕውሮች ያያሉ አንካሶችም ይሄዳሉ፥ ለምጻሞችም ይነጻሉ ደንቆሮችም ይሰማሉ፥ ሙታንም ይነሣሉ” — ማቴዎስ 11፥5።
  2. ሐዋርያ ጴጥሮስ “ጴጥሮስ ግን፦ ብርና ወርቅ የለኝም፤ ይህን ያለኝን ግን እሰጥሃለሁ፤ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሣና ተመላለስ አለው።”   — ሐዋርያት 3፥6። “ወደ ላይ ዘሎም ቆመ፥ ይመላለስም ጀመር፤ እየተመላለሰም እየዘለለም እግዚአብሔርንም እያመሰገነ ከእነርሱ ጋር ወደ መቅደስ ገባ።” — ሐዋርያት 3፥8። “ሕዝቡም ሁሉ እግዚአብሔርን እያመሰገነ ሲመላለስ አዩት፤”   — ሐዋርያት 3፥9። “መልካምም በሚሉአት በመቅደስ ደጅ ስለ ምጽዋት ተቀምጦ የነበረው እርሱ እንደ ሆነ አወቁት፤ በእርሱም ከሆነው የተነሣ መደነቅና መገረም ሞላባቸው።” — ሐዋርያት 3፥10። “ጴጥሮስም ሁሉን ወደ ውጭ አስወጥቶ ተንበርክኮም ጸለየ፥ ወደ ሬሳውም ዘወር ብሎ፦ ጣቢታ ሆይ፥ ተነሺ አላት። እርስዋም ዓይኖችዋን ከፈተች ጴጥሮስንም ባየች ጊዜ ተቀመጠች።”   — ሐዋርያት 9፥40። “ይህም በኢዮጴ ሁሉ የታወቀ ሆነ፥ ብዙ ሰዎችም በጌታ አመኑ።”   — ሐዋርያት 9፥42።
  3. ሐዋርያ ጳውሎስ ተአምራቱ: ፈውስ፣ ክፉ መናፍስት ማውጣት፣ ሙታን ማንሳት ጥቅስ: “እግዚአብሔርም በጳውሎስ እጅ ያልተለመዱ ተአምራት ያደርግ ነበር።” ሐዋርያት 19፥11 “ጳውሎስም ተዘርግቶ ወደ እርሱ ወደቀ… ሕይወቱ በእርሱ ውስጥ ነው።” ሐዋርያት ሥራ 20፥10
  4.  ፊልጶስ (ወንጌላዊ) ተአምራቱ: ክፉ መናፍስት ማውጣት፣ ፈውስ ጥቅስ: “ክፉ መናፍስት በታላቅ ድምፅ እየጮኹ ይወጡ ነበር… ብዙ ሽባዎችና አካል ጉዳተኞች ፈወሱ።”ሐዋርያት ሥራ 8፥7
  5. እስጢፋኖስ ተአምራቱ: ታላቅ ድንቅና ምልክት ጥቅስ: “እስጢፋኖስም በጸጋና በኃይል ተሞልቶ በሕዝቡ መካከል ታላቅ ድንቅና ምልክት ያደርግ ነበር።” ሐዋርያት 6፥8
  6. ሐዋርያት በአጠቃላይ ተአምራቱ: ብዙ ምልክቶችና ድንቅ ሥራዎች ጥቅስ: “በሐዋርያት እጅ ብዙ ምልክቶችና ድንቅ ነገሮች በሕዝቡ መካከል ይደረጉ ነበር።”ሐዋርያት 5፥12

በአጠቃላይ፦ እነዚህ ተአምራት፦ 

  1.  ወንጌልን ለማረጋገጥ
  2. የእግዚአብሔር ኃይል ለማሳየት
  3. ሰዎችን ወደ እምነት ለመመራት

አገልጋይ በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

+251902910126

አልባሾችህን ጠንቅቀህ እወቅ

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ

አልባሾችህን ጠንቅ ቀህእወቅ 

በአገልግሎት ዘመን እጅግ በብዙ ልንጠነቀቅ የሚገባው ነገር ቢኖር በአገልግሎት ዙሪያ አብረውኝ ያሉት እነማን ናቸው፣ አቋማቸውስ እንዴት ነው፣ አብረውኝ መከራ የሚቀበሉ ናቸው ወይስ መከራ አምጪ? በእርግጥ በአገልግሎት ዘመን እጅግ የቅርብ ናቸው የምንላቸው የመከራ አምጪ አሊያም አስመጪ ሊሆኑ ይችላሉ። አንዳንድ ጊዜ አብረኸኝ መከራ ተቀበል ብለን ልንጠራው የማንችል ሊኖር ይችላል፣ አብረኸኝ በጎ ወታደር ሆነህ መከራ ተቀበል የምንለው ላይኖር ይችላል። ብቻ ግን አቅምንና አቋምን ሳያስነኩ መዝለቁ እና የወንጌሉ ሥራ እንዲቀጥል እግዚአብሔር በጎኔ ቆሞ አበረታኝ እንዳለው ጳውሎስ ከሰው በላይ ሊረዳው የሚችል እግዚአብሔር እንዳለ ጠንቅቆ የሚያውቅ ሲሆን፣ የሚረዱት ወንድሞች ባይኖሩትም፣ ለምን መጣህ የልብህን ኩራት እናውቃለን ቢሉት ዳዊት ይህስ ትልቅ ስራ አይደለምን ማለቱ፣ ጎልያድን በተገዳደርከው በእግዚአብሔር ስም እመጣብሃለሁ ማለቱ ረዳቱ እግዚአብሔር እንደሆነ ጠንቅቆ ያውቃል። ለራእይህ ዘላቂነት፣ ታማኝ ተደርገህ ለተቆጠርክበት አገልግሎትህ መቃናት፣ ለአገልግሎትህ ድጋፍ ሰዎች ወሳኝ መሆናቸው እሙን ነው። ሆኖም ግን አጠገብህ ያሉ ሁሉ ለራእይህ፣ ለመጪው አገልግሎትህ መጥፋት አልያም መሳካት አስተዋጽኦ ሊኖራቸው ይችላል።

 1_አብሮ ተልኮ በተቃራኒየሚቆም

ሙሴ የሚወርሷትን ምድር ሊሰልሉ አስራ ሁለቱን ሰላዮች ቢልክም ከቀናት በኋላ የሥራ ግምገማ ምላሽ ከኢያሱና ከካሌብ በተቃራኒ በመቆም የሕዝቡን ልብ ማቅለጣቸው፣ ኢያሱና ካሌብ ግን ልብሳቸውን በመቅደድ ሕዝብን ሊያሳምኑ ታግለዋል። ሰው በመነሻ ሁሉም አንድ ነው፣ በምላሹ ግን ተቃራኒ እና ተፃራሪ ሊሆን ይችላል። አስር ተፃራሪ እንደሚኖር እና እንደማይጠፋ ልናውቅ ይገባል።

 2_የቤትህ ሰው ቤተሰብህ በጠላትነት ይቆማል

ህልም አለህ፣ ራእይ አለህ፣ ዕቅድ አለህ ግን አንድ ነገር ግን አለመርሳት እጅግ ተገቢ ነው። ሁልጊዜ ህልም ያለው በብልጫ መገለጡ አይቀሬ ስለሆነ ሁልጊዜ ዘወትር የህልም ተቃራኒዎች እና ጠላቶች እስከማጥፋት የሚደርሱ ስለሆነ ለህልምህ ዋጋ መክፈል አይቀሬ ነው። ዮሴፍ ከገጠሙት ችግሮች አንደኛው ህልሙ እንዳይሳካ ነው። ወንድሞቹ ያሉት እስኪ ህልሙ እንደሚሳካ እንያለን የሚል ምክርን በጥፋት ገልጠውታል። አስራ አንድ ተፃራሪ እንዳለ ማወቁ ተገቢ ነው። ግን የዮሴፍን ህልም አባቱ ብቻ ይጠብቀው ነበር። ብዙዎች የህልሜ ተጋሪ ነው ብሎ ማሰቡ ተላላነት ነው። ህልምህን የሚጠብቀው አንድ ብቻ ነው። አገልግሎት የአባቴ ልጆች ይደግፉኛል የምትለው አይደለም።

 3_ያመንካቸው ይንሸራተታሉ 

የውስጥ አቅምህ ምን ያህል ወሳኝ እና ሃገራዊ መሆኑን የማያውቁ ሊገፉህ፣ አንተ ውስጥ ያለው ለቅርቦችህ እንኳን እንደሚያስፈልግ ጨርሶ ላያውቁ ይችላሉ። ብዙውን ጊዜ ውስጥህ ያለውን የሚያውቁት የቅርቦች ሳይሆኑ የሩቆች፣ በአጠገብህ ያሉት አይደሉም። ዮፍታሔ ሊያጠፉት የነበራቸው አማራጭ ማንነቱን በሚነካ ንግግር በማጥፋት ነው። ሐሜት ነው? ወሬ ነው? አይቀሬ የክፉዎች የጦር መሳሪያ ናቸው። ወሬ ጥይቱ የማያልቅ ጠብመንጃ ነው። አንደበት፣ ክፉ አለም ጥይቷ የማያልቅ መሳሪያ ነች። ትገፋለህ ነገ ግን መፈለግህ አይቀሬ ነው። የምናምንቴ ልጅ መባል አይቀሬ ነው፣ የልዩ ሴት መባል አይቀሬ ነው። ለወሳኝ ጉዳይ ግን መፈለግ አይቀሬ ነው።

 4_የቅርብህ ያወርዱሃል

ታናሽ ነህ፣ ትንሽ ነህ መባል በእግዚአብሔር ዘንድ ግን የከበረ ነገር አለህ ተብለህ መታሰብህ ሰዎች ላይረዱህ፣ ላይገባቸው፣ ላያውቁት ይችላሉ። ውስጥህን የምታውቀው ግን አንተ እና እግዚአብሔር ብቻ ናችሁ። ታላላቆች ናቸው አዎ ይገፉሃል፣ የማይገፋህ በውስጥህ የራሱን አላማ ያስቀመጠ እግዚአብሔር ብቻ ነው። አንተ ብቻ እግዚአብሔር በውስጥህ ያስቀመጠው ትልቅ ጉዳይ እንደሆነና፣ ለሀገር፣ ለሕዝብ የሚጠቅም መሆኑን መረዳትና ማወቁ ተገቢ ነው። አንተን የማይመጥን ሞራልን የሚነካ ንግግር ሁሉ ሊደርስብህ እንደሚችል ማወቁ ተገቢ ነው።

በመጨረሻም

ለአገልግሎትህ አንዳንድ አልባሾችህን እጅግ ተጠንቀቅ። የማያንቀሳቅስ እና የማያራምድ ነገር ሊያለብሱህ ይችላሉ፣ ሆኖም ግን የራስህን ልምምድ ግን መረዳቱ ተገቢ ነው። ሳኦል ልብሱን ለዳዊት እንካ በዚህ ተዋጋ ማለቱ ያልፈተነውና የማያውቀው እንደሆነ መናገሩ እግዚአብሔር ያስለመደኝ አለ ማለቱ ነው። ያልፈተንከውን፣ ያልለመድከውን ከሚያለብስ፣ ለጊዜው ከሚያለብስህ ሽሽ። ለአገልግሎት ትልቅ ወዳጅ ሊሆን የሚችለው ለአንተም ወዳጅ የራእይህም ወዳጅ የሚሆን ሰው ነው። ዮናታን ለዳዊት ነገ አንተ ንጉስ መሆንህ አይቀርምና ብሎ ማለቱ ለእግዚአብሔርም፣ ለእርሱም፣ ለራእዩም ወዳጅነቱን እያሳየው ነው።

 የማያስኬድህን ከሚያሸክሙ ከሚያለብሱህ መሸሽ 

ብዙውን ጊዜ ፍሬያማ ከማያደርጉን የአንዳንዶች ልማድ ለእኛ የሚበጅና የሚያዋጣን ይመስለንና ተቀብለን በዚህ ልምምድ ልንቀጥል እና ልንሠራ እንጀምራለን። በሌላው ልምምድና ጥሪ አገልግሎት አይቀጥልም። የራስ ልምምድና ጥሪ እሱ ለአገልግሎታችን አዋጪ ነው። የሌላው ልምምድ የራሱ ነው፣ በራስ ጥሪ መቀጠሉ አዋጪ ነው፣ ዘላቂም ነው፣ የአላማና የግብ መጣመር በእርግጠኝነት ይታይበታል። “ዳዊትም ሰይፉን በልብሱ ላይ ታጠቀ፥ ገናም አልፈተነውምና መሄድ ሞከረ። ዳዊትም ሳኦልን፦ አልፈተንሁትምና እንዲህ ብዬ መሄድ አልችልም አለው። ዳዊትም አወለቀ።” — 1ኛ ሳሙኤል 17፥39።

በተለማመድከው ራእይህን አስጀምር አስቀጥል 

በአገልግሎት ዘመን ጅማሮ ከእግዚአብሔር ጋር ለብቻ የነበረ ቀደም ብሎ ያለ ልምምድ እጅግ ወሳኝነት አለው። ይኽም እግዚአብሔር በእኛ ሁኔታ ሊሠራበት የሚወደው ሥራ ነው። አንበሳና ድብ መቆራረጥና መግደል አስለምዶሃል? እሱን ይዘህ ቀጥል። በባዶ እጅ፣ በወንጭፍ አለማምዶሃል? እሱን ይዘህ ቀጥል። “በትሩንም በእጁ ወሰደ፥ ከወንዝም አምስት ድብልብል ድንጋዮችን መረጠ፥ በእረኛ ኮረጆውም በኪሱ ከተታቸው፤ ወንጭፍም በእጁ ነበረ፤ ወደ ፍልስጥኤማዊውም ቀረበ።” — 1ኛ ሳሙኤል 17፥40።

 ከሚደግፉህና ከራእይህ ጎን ከሚቆሙት ጋር ቀጥል

በውስጥህ ያለውን አቀጣጥል፣ በአደራ የተቀበልከውን ቸል አትበል፣ በውስጥ ያለውን እሳት አቀጣጥል ከሚል የተቀበልከውን አደራ ተጠንቀቅለት ከሚልህ ጎን መጣመር እና መጠመድ እሱ አዋጪ ነው። “ዮናታንም የለበሰውን ካባ አውልቆ እርሱንና ልብሱን ሰይፉንም ቀስቱንም መታጠቂያውንም ለዳዊት ሸለመው።” — 1ኛ ሳሙኤል 18፥4።

ወንድም በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

+251902910126

የትውልድ አደራ

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ

 

የትውልድ አደራ

የትውልድ ባለአደራነትን መወጣት

አደራ ለአንድ የተወሰነ ተግባር እና ክዋኔ ወይም ግዴታ ለአንድ ሰው ሃላፊነት ወይም ስልጣን መስጠት መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን፣ የተሰጠውን ኃላፊነት በብቃት እና በኃላፊነት እንዲወጣ እምነትን መጣል ሲሆን፣ አደራ የአደራን ተግባር በአደራ፣ በመተማመን እና በአደራ የተሰጠው ሰው አቅም ላይ በማመን ላይ የተመሰረተ ሊሆን ይችላል። 

 

አደራን የመወጣት እና አደራን ከግብ ማድረስ እንዴት ያለ መታደል ነው። በተለይ የትውልድን አደራ ተቀብሎ ትውልድ በመልካም መንገድ የእግዚአብሔርን ሕግ ተከትሎ እንዲሄድ አድርጎ እና በዚህም ፍሬን ማየት እንዴት እጅግ ያስደስታል። 

ትውልድን ከክፋት ነጥሎ ትውልድን በእውነት መንገድ እንዲሄዱ ማድረግ፣ ከእግዚአብሔርም ጋር ማገናኘት እንዴት አይነት ትልቅ ሥራ ነው? በእውነት መንገድ ሄደውም ማየትን የመሠለ ነገር የለም። 

በተለይ በትውልድ ላይ በእውነትና በሐቅ እየለፉ፣ እየታተሩ ያሉ ምን ያህል ለውጤት እንደሚተጉ ሲታዩ የጭንቀታቸውን ልክ በጥቂቱ መገመት የሚቻል ቢሆንም እውነታውን የሚረዳው አይነቱ እና እራሱ ባለቤቱ ነው። 

አለም የራሷን ትውልድ ገዳይ አሰናድታ ባስቀመጠችበት ዘመን ቤተክርስቲያን በመዘናጋት ለገዳይ እድልን መስጠቷ ከመዘናጋቷም የተነሳ አጥፊው እየተጋ ባለበት ዘመን አለመንቃት የነገ ተስፋዎቿ እየተነጠቁባት መሆኑ ለአፍታም ግድ ያላላት ምን ልትሠራ? ሥራዋስ ምን እንደሆነ ጠንቅቃ አለማወቋ ትውልድ ከማህፀን ጀምሮ እየመከነ መሆኑ አለመረዳቷ የነገ የቤተክርስቲያን ተስፋዋ ጭምር እየጠፋ መሆኑን አሳሳቢ ጉዳይ ሆኖአል። “የግብፅም ንጉሥ አንዲቱ ሲፓራ ሁለተኛይቱም ፉሐ የሚባሉትን የዕብራውያንን አዋላጆች እንዲህ ብሎ ተናገረ።” — ዘጸአት 1፥15። “እናንተ የዕብራውያንን ሴቶች ስታዋልዱ፥ ለመውለድ እንደደረሱ ባያችሁ ጊዜ፥ ወንድ ቢሆን ግደሉት ሴት ብትሆን ግን በሕይወት ትኑር።” — ዘጸአት 1፥16። “የግብፅም ንጉሥ አዋላጆችን ጠርቶ፦ ለምን እንዲህ አደረጋችሁ? ወንዶቹን ሕፃናትንስ ለምን አዳናችሁ? አላቸው።”— ዘጸአት 1፥18። የነቁትም ቢሆን እጅግ ጥቂት መሆናቸውና ሥራውም ሰፊ ከመሆኑ አኳያ አለመጣጣሙ ትውልድን ከጥፋት መመለሱ በበቂ ሁኔታ እየተሠራ አለመሆኑ ትልቁ ማሰያና ማረጋገጫ ነው። “አዋላጆች ግን እግዚአብሔርን ፈሩ፥ የግብፅ ንጉሥም እንዳዘዛቸው አላደረጉም፥ ወንዶቹን ሕፃናትንም አዳኑአቸው።” — ዘጸአት 1፥17። “አዋላጆቹም ፈርዖንን፦ የዕብራውያን ሴቶች እንደ ግብፅ ሴቶች ስላልሆኑ፤ እነርሱ ጠንካሮች ናቸውና አዋላጆች ሳይገቡ ስለሚወልዱ ነው አሉት።” — ዘጸአት 1፥19።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር በነበረበት ዘመን ለትውልድ ያለውን የጠለቀ ፍቅሩን የገለጠበት መንገድ የሁላችን አእምሮ ውስጥ ያለ ነው። ህፃናት የነገ ተስፋዎች መሆናቸውን ከተናገረበት ንግግር አኳያ መረዳት ይቻላል። ብዙውን ጊዜ ትልልቆች በተሠበሰቡበት የትኛውም ስፍራ ህፃናት እንዲደርሱ አሊያም እንዲገኙ ጨርሶ አይፈቀድላቸውም። "ልጅ ያቦካው ለእራት አይበቃም" በሚል ከንቱ ብሂል ህፃናትን እናሳንሳለን፣ እንዲጠጉንም አንሻም፣ አናምናየውም። በእርሪልጅ ባለበት ጥፋት እንደማይጠፋ ይታወቃል፣ አርቆ ማሳደጉ የእኛ ድርሻ ነው፣ ከአይናችንም ባይርቁ መልካም ነው።

ጌታ ኢየሱስና ጴጥሮስ
ዮሐንስ 21:15፣ ለጴጥሮስ የተሰጠው የትውልድ አደራ የሁሉንም የዕድሜ ክልል ያካተተ ሲሆን፣ በተለይ "ቤተክርስቲያኔን በአንተ ላይ እመሰርታለሁ" ማለቱ ምን ያህል ቤተክርስቲያን የትውልድን አይነት ይዛ እንደምትገኝ ማሳያ ነው። ለዚህም ነው ለጴጥሮስ የተሠጠው የትውልድ አደራ ከብዶና በተደጋጋሚ መጠየቁ የጉዳዩ የአደራ ክብደቱን፣ አሳሳቢነትና ኃላፊነትን የሚያሳየው። ስለዚህ በአደራ ባለቤትና ሰጪው ልክ ተረድተን አደራን መወጣት አለብን። ለውጤታማነትና ለፍሬያማነቱም መትጋቱም ጭምር ታሳቢ ማድረጉ መልካም ነው። ቆጥሮ የሰጠን ቆጥሮ ይረከበናል።

መልዕክተኛው_ዮሐንስና_ልጆቹ
የአንደኛ፣ ሁለተኛ፣ ሶስተኛ መልዕክት ፀሐፊው
ዮሐንስ ከመልዕክቱ እንደምንረዳው ምን ያህል ከስሩ ባሉት ላይ እንደሠራና ተደስቶም  ስለ እነርሱ ከሌሎች የሰማውን ምስክርነት፣ የተመሰከረውን በመጥቀስ መናገሩ የልፋቱን ውጤት ማየቱ እንዳስደሰተው በመልዕክቱ ሲናገር እናየዋለን። የልፋቱን ልክ በዙሪያቸው ባሉት ሰዎች ምስክርነት መሠጠቱ የዘራውን ዘር በሌሎች ዘንድ ተዘርቶ ማየቱ እና ፍሬው ወደ ሌሎች መሻገሩ ምን ያህል ደስታን እንዳጫረበት መመልከት ይቻላል።  “ሽማግሌው በእውነት እኔ ለምወደው ለተወደደው ለጋይዮስ።”— 3ኛ ዮሐንስ 1፥1።

“ወንድሞች መጥተው አንተ በእውነት እንደምትሄድ ስለ እውነትህ ሲመሰክሩ እጅግ ደስ ብሎኛልና።” — 3ኛ ዮሐንስ 1፥3። “ለድሜጥሮስ ሁሉ ይመሰክሩለታል፥ እውነት ራስዋም ትመሰክርለታለች፤ እኛም ደግሞ እንመሰክርለታለን፥ ምስክርነታችንም እውነት እንደ ሆነ ታውቃላችሁ።” — 3ኛ ዮሐንስ 1፥12። “ልጆቼ በእውነት እንዲሄዱ ከመስማት ይልቅ የሚበልጥ ደስታ የለኝም።” — 3ኛ ዮሐንስ 1፥4።

ዛሬስ በዚህ ዘመን ያለን እግዚአብሔርን እና የእግዚአብሔርን ሕዝብ የምናገለግል፣ አደራ የተሰጠን በእርግጥ የቀደሙት አባቶች እንዳደረጉት ዛሬም እንዲሁ እያደረግን ይሆን? የትውልድን አደራ ተሸክመን ያለን ተገቢውን ነገር እያደረግን ይሆን?

“ልጆቼ ሆይ፥ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ኃጢአተኛ በማድረጋችሁ ስለ እናንተ የደረሰኝ ወሬ መልካም አይደለምና ይህ አይሆንም።” — 1ኛ ሳሙኤል 2፥24።

 ትናንት ትውድን ሊያጠፋ የሞከረ ፈርኦን በቀጣይ በሄሮድስ የቀጠለው ዛሬም ትውልድን ሊያጠፋ የተዘጋጀ መልኩንም፣ ስሙን፣ አይነቱንም፣ አሰራሩንም ቀይሮ የተዘጋጀ መኖሩን ለቅፅበት መርሳት የለብንም። ይልቁን መልኩን ቀይሮ በመምጣት ትውልድን ለራሱ ሊማርክና ብሎም ሊያጠፋ የቆረጠን የጨለማ ተልዕኮ አስፈፃሚን እኛ በእግዚአብሔር ፊት በምናደርገው የትኛውም ትጋት ተልዕኮውን እንደምናፈርስ መዘንጋት የለብንም።

የቤተክርስቲያን_መሪና_ተተኪ_ትውልድ

 ዛሬ ላይ በዚህን ጊዜ የቤተክርስቲያን ተልዕኮ ሙሉ በሙሉ በይሆንም እጅግ በአብዛኛው የነገ ተስፋ የሆኑት ትውልድ   ላይ እየሰራን አለመሆኑ አልታወቀንም። እየሠሩ ነው የሚባል መከራከሪያ ነጥብ እንኳን ቢነሳ ተልዕኮውና አላማው       ከራስ ጥቅምና ፍላጎት የተነሳ እንጂ የትውልድ አደራነት ተሰምቶት የሚሠራው እጅግ ጥቂት ነው። "የመከሩ ሠራተኞች ጥቂቶች ናቸው" የሚለውን የእግዚአብሔርን ቃል ማሰቡ እጅግ ተገቢ ነው። 

መሪነት አንድም በደጅ አንድም በቢሮ ተቀምጠን ብቻ የምንሠራው ሥራ አይደለም። ለተጠራንበት አላማ ለግቡ መሳካት አውራውን ሥራ መሥራት አለብን። የፈዘዘ፣ የደነዘዘ በምንም አይነት መልኩ ሥራ አይሠራም፣ አጥፊ ትውልድን እንኳን በቅጡ አይመክርም፣ አይገስፅም፣ አይቆጣም፣ ልጆችህ እንዲህ አደረጉ ቢባል እንኳን "እግዚአብሔር የወደደውን ያድርግ" በሚል ሽንፈትና ተስፋ መቁረጥን ያዘለ ከመፍትሔ መሸሻና ማምለጫ ሃሳብን በመሰንዘር ጉዳዩን ወደ ጎን መተው መጨረሻው አያምር አይነት ይሆናል። ትውልድን የሚያረክስና የሚያበላሽ ትውልድ ከመምጣቱ በፊት በእጅ ያለን ትውልድ ከወዲሁ አርቆ ማስተካከሉ መሠረቱን ማስተካከል እንደሆነ ማወቅ ይጠቅመናል። ነገን ዛሬ ላይ እንሥራ። 

ካህኑ ኤሊ እና ልጆቹ

“ዔሊም እጅግ አረጀ፤ ልጆቹም በእስራኤል ሁሉ ላይ ያደረጉትን ሁሉ፥ በመገናኛውም ድንኳን ደጅ ከሚያገለግሉት ሴቶች ጋር እንደ ተኙ ሰማ።” — 1ኛ ሳሙኤል 2፥22። ጥፋተኛን አይተን፣ ስለጥፋተኛ ሰምተን "ጆሮ ዳባ ልበስ"፣ "የዝሆን ጆሮ ይሰጠን" ባንል መልካም ነው። “እርሱም አላቸው፦ ስለ ክፉ ሥራችሁ ከዚህ ሕዝብ ሁሉ ሰምቻለሁና ስለምን እንዲህ ያለ ነገር ታደርጋላችሁ?”— 1ኛ ሳሙኤል 2፥23።
“ልጆቼ ሆይ፥ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ኃጢአተኛ በማድረጋችሁ ስለ እናንተ የደረሰኝ ወሬ መልካም አይደለምና ይህ አይሆንም።” — 1ኛ ሳሙኤል 2፥24። እግዚአብሔር ከምናምንቴዎች ጋር እንደማይሠራ ልብ ልንል ይገባል።

ነቢዩ ሳሙኤል እና ልጆቹ

ነብይ ሳሙኤል በዘመኑ ሀገር ምድር ያረፈችበት፣ እግዚአብሔርም ያረፈበት፣ እስራኤል ከጠላቱ ከፍልስጥኤማውያን ያረፈችበት ትልቅ ነብይ የነበረ በሞቱ እንኳን እስራኤል ለቀናት ያለቀሰችለት ትልቅ ነብይ ነበረ። (እንዲህ አይነት መሪ ይስጠን! አሜን!) የነብዩ ሳሙኤል ልጆች ግን እሱ በሄደበት መንገድ ልክ አልሄዱም። በአባታቸው እግር ተተክተው ያገለግላሉ ተብለው የተሾሙና የተቀመጡ አባታቸው በሕይወት ዘመኑ ያልሄደበትን መንገድ በመሄድ እግዚአብሔር በማይፈልግበት መንገድ ሕዝብ እንዲሄድ ከደረጉ፣ የሕዝብንም ልብ ከእግዚአብሔር አሸፈቱ፣ የአህዛብን ስረዓት እንዲመኙ አደረጉ።  “እነሆ፥ አንተ ሸምግለሃል፥ ልጆችህም በመንገድህ አይሄዱም፤ አሁንም እንደ አሕዛብ ሁሉ የሚፈርድልን ንጉሥ አድርግልን አሉት።” — 1ኛ ሳሙኤል 8፥5። “የሚፈርድልንም ንጉሥ ስጠን ባሉት ጊዜ ነገሩ ሳሙኤልን አስከፋው፤ ሳሙኤልም ወደ እግዚአብሔር ጸለየ።” — 1ኛ ሳሙኤል 8፥6።
       

              በመጨረሻም:-
የመፍትሄ_ሐሳብ፡ 
1. የሚሄድበትን መንገድ መምራት
       1.1. ከእግዚአብሔር ቃል ጋር ማገናኘት
እጅግ ከማቅረብና ከመቅረብ በቀጠለ ትውልድ ከእግዚአብሔር ቃል ጋር ማቆራኘት፣ እንዲጠብቅና እንዲያሰላስል ማድረግ። “ልጄ ሆይ፥ ሕጌን አትርሳ፥ ልብህም ትእዛዛቴን ይጠብቅ።” — ምሳሌ 3፥1።

ልጅን አግባብ በሆነ መልኩ ከእግዚአብሔር ቃል አኳያ ማስተማር፣ ለነገ እንደሚጠቅመው እና የእግዚአብሔር ቃል ዋስትና እንደሆነ ማሳየት። 

   1.2. ልጅን ማሰልጠን፣ ማስተማር
“ልጅን በሚሄድበት መንገድ ምራው፥ በሸመገለም ጊዜ ከእርሱ ፈቀቅ አይልም።” — ምሳሌ 22፥6።

“Train up a child in the way he should go: and when he is old, he will not depart from it.” — Proverbs 22፥6 (KJV)

2.  ከእግዚአብሔር ቃል ጋር ማገናኘት
ኢያሱና ሰለሞን የተነገራቸው የእግዚአብሔር ቃል ምክር ሲነገራቸው የነገን፣ የወደፊቱን ነገራቸው የሚሳካው በእግዚአብሔር ቃል ላይ በመመርኮዝ ብቻ እንደሆነ አጠንክረው ነገረዋቸዋል።

    2.1. እግዚአብሔር ሙሴ ለኢያሱ የነገረውን ኢያሱን ሲያስታው፦
“ነገር ግን ጽና፥ እጅግ በርታ፤ ባሪያዬ ሙሴ ያዘዘህን ሕግ ሁሉ ጠብቅ፥ አድርገውም፤ በምትሄድበትም ሁሉ እንዲከናወንልህ ወደ ቀኝም ወደ ግራም አትበል።” — ኢያሱ 1፥7። 

    2.2. ዳዊት ልጁን ሰለሞንን የመከረው ምክር
“በርታ ሰውም ሁን፤ የምታደርገውንና የምትሄድበትን ሁሉ ታከናውን ዘንድ፥ በሙሴ ሕግ እንደ ተጻፈ ሥርዓቱንና ትእዛዛቱን ፍርዱንና ምስክሩንም ትጠብቅ ዘንድ፥ በመንገዱም ትሄድ ዘንድ፥ የአምላክህን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ጠብቅ።” — 1ኛ ነገሥት 2፥3።

3. በአደራነትና በኃላፊነት መምራት
መፅሐፍ ቅዱሳችን በትውልድ ላይ የአደራነትን ተልዕኮ የተሰጠው ሐዋሪያው ጴጥሮስ ተደጋግሞ የተነገረው ጉዳይ ቢኖር በእያንዳንዱ የዕድሜ ደረጃ ያሉትን ምን እንዲያደርግላቸው እንደሚገባ ጌታችን ኢየሱስ በመንገርና አደራን በመስጠት ነግሮታል። ዛሬም በዚህ ዘመን ላለን ይህንኑ አደራ እንደተቀበልን ማወቅ አለብን። ዮሐንስ 21:15-18 መመልከት ይቻላል።

4. ቤተሰባዊ ምክር መለገስ
ንጉስ ዳዊት ልጁን ሰለሞንን አንድም እንደ ሃገር መሪ፣ አንድም እንደ ወላጅ አባት ምክሩን ከእግዚአብሔር ቃል አኳያ ነግሮታል። አደራውን ተወጣ። “በርታ ሰውም ሁን፤ የምታደርገውንና የምትሄድበትን ሁሉ ታከናውን ዘንድ፥ በሙሴ ሕግ እንደ ተጻፈ ሥርዓቱንና ትእዛዛቱን ፍርዱንና ምስክሩንም ትጠብቅ ዘንድ፥ በመንገዱም ትሄድ ዘንድ፥ የአምላክህን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ጠብቅ።” — 1ኛ ነገሥት 2፥3። “እናንተም አባቶች ሆይ፥ ልጆቻችሁን በጌታ ምክርና በተግሣጽ አሳድጉአቸው እንጂ አታስቆጡአቸው።” — ኤፌሶን 6፥4። “እኔም ዛሬ አንተን የማዝዘውን ይህን ቃል በልብህ ያዝ።” — ዘዳግም 6፥6። “ለልጆችህም አስተምረው፥ በቤትህም ስትቀመጥ፥ በመንገድም ስትሄድ፥ ስትተኛም፥ ስትነሣም ተጫወተው።” — ዘዳግም 6፥7።

አደራን መወጣት ይሁንልን!
በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

የተፅእኖ ሰው

Details
Written by: BEREKET SULAMO SUGEBO
Category: The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ

የተፅእኖ ሰው

እነርሱ በእምነት መንግስታትን ድል ነሡ ጽድቅን አደረጉ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ

ዕብራውያን 11፡33

በምድራችን ላይ በየትኛውም ዘመን በታሪክ መዛግብት እና በአፈ ታሪክ እንደሚነገረን፣ ከኖርንባቸው ዘመናት ቀድመው የኖሩ በፍልስፍናቸው አመለካከት ይሁን፣ በÞለቲካ አመለካከታቸውና ፍልስፍናቸው ይሁን፣ በፈጠራ ሥራና ግኝት ልህቀት ይሁን፣ ብቻ በተሰማሩበት በየትኛውም ዘርፍ ተፅዕኖን ፈጥረው ለዓለም የሚጠቅም አዎንታዊ ይሁን፣ የማይጠቅም አሉታዊ ጉዳይ ይሁን ሰርተው አልፈዋል፣ አንቱታንም ተችረው፣ ተሞግሰው ለበጎ ነገር ይሁን ለዕኩይ አንድ አሻራ ጥለው አልፈዋል፡፡

Read more: የተፅእኖ ሰው

ያልተጎሰመ አንደበት

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ


tongue

ያልተጎሰመ አንደበት

“አንደበትህን ከክፉ ከልክል፥ ከንፈሮችህም ሽንገላን እንዳይናገሩ።”— መዝሙር 34፥13። 

በአለም ላይ የተደረጉ የትኛውም አይነት ጦርነቶች በቅድሚያ ውጊያን የጀመሩት በዘመናቸው በነበሩት የመገናኛ ዘዴዎች በመጠቀም በአንደበት ነው። ክፉ አንደበት የጠብ ጫሪነትን ሚና በከፍተኛ ደረጃ የምትወጣ የክፉ አለም ተምሳሌት ነች። የጦርነት ክተት ይሁን አዋጅ በነጋሪት ጉሰማ ሲታወጅ አንደበት የጦርነትን መጀመር ፋና ወጊና ፈር ቀዳጅ አንደበት ነው። በአንደበት በትንሽ ምላስ የተጫረ የጦርነት ምላጭ ተኩስ የተጀመረው በዚህ በአንደበት አለም ነው። 

በክርስትናውም አለም እንዲሁ ያልተጎሰመ አንደበት ሥራው ይኸው ሲሆን በተለይ በወንድማማች መካከል ጠብን በመዝራት የሚታወቀው ይኸው ያልተገራው አንደበት ነው። በተለይ በዚህ ባለንበት ዘመን እጅግ ብዙ አገልጋዮች በድብደባና በዱላ ከመሰበር በላይ በአንደበት የተሰበሩት ኅልቁ መሳፍርት ናቸው። 

በብሉይ ኪዳን ዘመን እንኳን ስንመለከት ሙሴ ከላካቸው አስራ ሁለቱ ሰላዮች የአስሩ መረጃ የሕዝበ እስራኤልን ልብ ያቀለጠ መረጃ ነበር። በተለይ ከአፋቸው የሚወጣው ንግግር የሕዝቡ ልብ እስኪቀልጥ ድረስ እና በሙሴና በእግዚአብሔር ላይ እስኪነሱ ድረስ ያደረሰን ተገቢ ያልሆነን መረጃ ይዘው በመምጣት የህዝብን ልብና ጉዞ አውከዋል። “ከእኔ ጋር የወጡ ወንድሞቼ ግን የሕዝቡን ልብ አቀለጡ፤ እኔ ግን አምላኬን እግዚአብሔርን ፈጽሜ ተከተልሁ።” — ኢያሱ 14፥8። 

የብዙዎች ሕይወትና አገልግሎት እንዲሁም ሩጫቸው የተቃጠለውና የተመታው በአንደበት አለም በተደረገው ጦርነት ነው። በሰውነታችን ላይ ካሉት ብልቶቻችን ወይም የሰውነት ክፍሎቻችን መካከል እጅግ አደገኛው አካል ወይም ብልት አንደበት ነው። አጥንት እስኪሰበር የሚያደርስን ክፋት የተሞላ መርዛማ ነገር ነው። 

“እንዲሁም አንደበት ደግሞ ትንሽ ብልት ሆኖ በታላላቅ ነገር ይመካል። እነሆ፥ ትንሽ እሳት እንዴት ያለ ትልቅ ጫካ ያቃጥላል።”— ያዕቆብ 3፥5። 

“አንደበትም እሳት ነው። አንደበት በብልቶቻችን መካከል ዓመፀኛ ዓለም ሆኖአል፤ ሥጋን ሁሉ ያሳድፋልና፥ የፍጥረትንም ሩጫ ያቃጥላል፥ በገሃነምም ይቃጠላል።”— ያዕቆብ 3፥6።


በተለይ በመፅሐፍ ቅዱሳችን ስለ አንደበት የተነገረው ቃል እጅግ አሉታዊ በሆነ መንገድ የተገለጸው ነው። ስለ አንደበት በዝርዝር በማንነቱና በባህሪው የተገለጠበት መንገድ፦
1. ትንሽ ብልት
2. በታላላቅ ነገር ይመካል
3. እሳት 
4. ዓመፀኛ አለም
5. ሥጋን የሚያሳድፍ
6. ሩጫን የሚያቃጥል
7. በገሃነምም የሚቃጠል እንደሆነ በግልፅ ተቀምጧል። 

በተለይ በነህምያ እና በዕዝራ ዘመን የፈረሰችውን እየሩሳሌምን በሚጠግኑበት ጊዜ በዙሪያቸው የነበሩት ጠላቶቻቸው የመጀመሪያውን ጦርነት የጀመሩት በአንደበት ጦርነት በሚያናንቅና በሚያጥላላ ንግግር ነው። “አሞናዊውም ጦብያ በአጠገቡ ቆሞ፦ በድንጋይ በሚሠሩት ቅጥራቸው ላይ ቀበሮ ቢመጣበት ያፈርሰዋል አለ።” — ነሀምያ 4፥3። አንደበት የዚህን ያህል ውስጥን የሚያበግን ንግግርን አፍልቆ ስሜትን ይነካል። ለዚህ ነው ነህምያ በምላሹ፦ “አምላካችን ሆይ፥ ተንቀናልና ስማ፤ ስድባቸውን በራሳቸው ላይ መልስባቸው በምርኮ አገር ለብዝበዛ አሳልፈህ ስጣቸው።” — ነሀምያ 4፥4። “በደላቸውንም አትክደን፥ ኃጢአታቸውም ከፊትህ አይደምሰስ፤ በሠራተኞች ፊት አስቆጥተውሃልና።” — ነሀምያ 4፥5። 

የአለማውያኑ ንግግር ይህን ያህል ላይጎዳ ይችላል፣ ምክንያቱም የባህሪያቸው ስለሆነ ቦታ ላንሰጠው እንችል ይሆናል። ሆኖም ግን በእኛ በክርስቲያኖች መካከል የሚደረገው የአንደበት ላይ ጦርነቶች በብዙ አኅዛብ መካከል መሳለቂያ እስከመሆን ደርሰናል። በተለይ በመፅሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ ላይ ያለን የሰፋ ልዩነትና የምንሰጣጣቸው ምላሾች በብዙዎች ዘንድ አስተችቶናል። የአንደበታችን አለመገራት በብዙዎች ዘንድ እምነታችን እንዲተችና እንዲነቀፍ መንስኤ እና ምክንያት ሆኖአል። ስለዚህ የአንደበታችንን ጉዳይ እጅግ በአፅንኦት ልንመለከተው ይገባል። በተለይ ከምናለማው በላይ የምናቃጥለው በዝቷል። 

“ነገር ግን አንደበትን ሊገራ ማንም ሰው አይችልም፤ የሚገድል መርዝ የሞላበት ወላዋይ ክፋት ነው።”— ያዕቆብ 3፥8። አንደበታችንን በራሳችን አቅም ልንገራውና ልንቆጣጠረው ባንችልም፣ እግዚአብሔር እራሱ ጠባቂ ያኑርልን። 

  1. ጉዞን ያውካል፦ ያልተጎሰመ አንደበት በሕይወት እያደረግን ያለነውን ማንኛውም ነገር የማወክ ኃይል አለው። 
    አንደበት፦ በተለይ ወሬ ከታከለበት የሌሎችን አቋም የመሸርሸርና የማውረድ አቅም አለው። “ስለ ሰለሉአትም ምድር ክፉ ወሬ ለእስራኤል ልጆች እያወሩ፦ እኛ ዞረን የሰለልናት ምድር የሚኖሩባትን ሰዎች የምትበላ ምድር ናት፤ በእርስዋም ዘንድ ያየናቸው ሰዎች ሁሉ ረጃጅም ሰዎች ናቸው።” — ዘኍልቁ 13፥32። 
  2. ከመሪ ያጣላል፦ በተለይ በአንድ ህብረት ውስጥ ያለ አንደበቱ ያልተጎሰመ አካል ሕብረቱን የማናጋትና ከመሪ ጋር የማጋጨት ብቃት አለው። ይህም ሲሆን ዓላማ እና ግብ ከስኬት እንዳይደርስ እንቅፋትና መሠናክልን ያደርጋል። “ምድሪቱንም ሊሰልሉ ሙሴ ልኮአቸው የተመለሱት ሰዎች ክፉ ወሬም ስለ ምድሪቱ እያወሩ በእርሱ ላይ ማኅበሩ ሁሉ እንዲያጕረመርሙ ያደረጉ፥”— ዘኍልቁ 14፥36። “ክፉ ወሬ ያወሩ እነዚያ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት በመቅሠፍት ሞቱ።” — ዘኍልቁ 14፥37። 

አንደበታችንን መጠቀም ያለብን መጥፎ ቃላትን ከመናገር መከልከል ብቻ ሳይሆን መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያስተምረን የሚጠቅመውን ለመናገርም ነው። በመጽሐፍም “ለሚሰሙት ጸጋን ይሰጥ ዘንድ፥ እንደሚያስፈልግ ለማነጽ የሚጠቅም ማናቸውም በጎ ቃል እንጂ ክፉ ቃል ከአፋችሁ ከቶ አይውጣ።”— ኤፌሶን 4፥29። 

ያልተጎሰመ አንደበት፦ አምልኮአችንን፣ እምነታችንን የሚያስነቅፍ፣ የሚያስተች፣ የሚያጎድፍ ነው። ስለዚህ፦ ቅዱስ ያዕቆብ ‹‹አንደበቱን ሳይገታ፥ ልቡን እያሳተ እግዚአብሔርን የሚያመልክ የሚመስለው ማንም ቢኖር፥ እርሱ አምልኮቱ ከንቱ ነው›› በማለት የተናገራቸው ቃላት ባልተገደበ አንደበት ምክንያት የአንድ ሰው የክርስትና ህይወት እና አምልኮ እንዴት ከንቱ ሊሆን እንደሚችል ያመላክታል። ክርስትና ያለ ትህትናና ምግባር ከንቱ በመሆኑ የማንተገብራቸውን ተግባራት በተዋቡ ቃላት ከሽነንና አጅበን በሽንግላ አንደበት በስመ ክርስቲያን ብቻ መኖር የተገባ አይደለም፡፡ “አንደበቱን ሳይገታ ልቡን እያሳተ እግዚአብሔርን የሚያመልክ የሚመስለው ማንም ቢኖር የእርሱ አምልኮ ከንቱ ነው።”— ያዕቆብ 1፥26። 

በሐዋርያው ያዕቆብ እንደገለጸው ከቁጥጥር ውጭ የሆነ አንደበት ወደ ኃጢአት ይመራል፡፡ አንድ ሰው ምላሱን ሳይገታ፣ በክፉ እሳቤ ተነሣስቶ ቃላትን ቢያወጣ በመንፈሳዊ ሕይወት ውስጥ እክል ይሆንበታል። አምልኮው፣ አገልግሎቱ እና ልፋቱ ሁሉ መና ይሆናል። እምነት በጎደለውና በሐሰተኛ አንደበት የእውነትን ቃላት ብናወጣ የእግዚአብሔርን ሕግ አለማክበር በመሆኑ የጽድቅ ሳይሆን የኵነኔ ፍርድ ይከተለናል፡፡ “ክፉ ወሬ ያወሩ እነዚያ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት በመቅሠፍት ሞቱ።” — ዘኍልቁ 14፥37።

በመጨረሻም፦
ስለዚህ የሰውነት አካለለችን መካከል አንደበት የማንነት መገለጫ ነው። ልንጠብቀው የሚገባ የሰውነታችን ክፍል ነው። ካልጠበቅነው ውርደታችንን የሚያፈጥን የሰውነታችን ክፍል ነው ።እግዚአብሔር የሚከብርበት እኛም የምንከብርበት ወይንም ከክብር የምንዋረድበት የሰውነታችን አካል ማለት ነው። “ሞትና ሕይወት በምላስ እጅ ናቸው፤ የሚወድዱአትም ፍሬዋን ይበላሉ።”
  — ምሳሌ 18፥21። 

“አቤቱ፥ ለአፌ ጠባቂ አኑር፥ የከንፈሮቼንም መዝጊያ ጠብቅ።” — መዝሙር 141፥3። 

“አቤቱ፥ ረድኤቴ መድኃኒቴም፥ የአፌ ቃልና የልቤ አሳብ በፊትህ ያማረ ይሁን።” — መዝሙር 19፥14። 

እግዚአብሔር ይባርካችሁ!
አገልጋይ በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

ያልተጎሰመ አንደበት

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ


tongue

ያልተጎሰመ አንደበት

“አንደበትህን ከክፉ ከልክል፥ ከንፈሮችህም ሽንገላን እንዳይናገሩ።”— መዝሙር 34፥13። 

በአለም ላይ የተደረጉ የትኛውም አይነት ጦርነቶች በቅድሚያ ውጊያን የጀመሩት በዘመናቸው በነበሩት የመገናኛ ዘዴዎች በመጠቀም በአንደበት ነው። ክፉ አንደበት የጠብ ጫሪነትን ሚና በከፍተኛ ደረጃ የምትወጣ የክፉ አለም ተምሳሌት ነች። የጦርነት ክተት ይሁን አዋጅ በነጋሪት ጉሰማ ሲታወጅ አንደበት የጦርነትን መጀመር ፋና ወጊና ፈር ቀዳጅ አንደበት ነው። በአንደበት በትንሽ ምላስ የተጫረ የጦርነት ምላጭ ተኩስ የተጀመረው በዚህ በአንደበት አለም ነው። 

በክርስትናውም አለም እንዲሁ ያልተጎሰመ አንደበት ሥራው ይኸው ሲሆን በተለይ በወንድማማች መካከል ጠብን በመዝራት የሚታወቀው ይኸው ያልተገራው አንደበት ነው። በተለይ በዚህ ባለንበት ዘመን እጅግ ብዙ አገልጋዮች በድብደባና በዱላ ከመሰበር በላይ በአንደበት የተሰበሩት ኅልቁ መሳፍርት ናቸው። 

በብሉይ ኪዳን ዘመን እንኳን ስንመለከት ሙሴ ከላካቸው አስራ ሁለቱ ሰላዮች የአስሩ መረጃ የሕዝበ እስራኤልን ልብ ያቀለጠ መረጃ ነበር። በተለይ ከአፋቸው የሚወጣው ንግግር የሕዝቡ ልብ እስኪቀልጥ ድረስ እና በሙሴና በእግዚአብሔር ላይ እስኪነሱ ድረስ ያደረሰን ተገቢ ያልሆነን መረጃ ይዘው በመምጣት የህዝብን ልብና ጉዞ አውከዋል። “ከእኔ ጋር የወጡ ወንድሞቼ ግን የሕዝቡን ልብ አቀለጡ፤ እኔ ግን አምላኬን እግዚአብሔርን ፈጽሜ ተከተልሁ።” — ኢያሱ 14፥8። 

የብዙዎች ሕይወትና አገልግሎት እንዲሁም ሩጫቸው የተቃጠለውና የተመታው በአንደበት አለም በተደረገው ጦርነት ነው። በሰውነታችን ላይ ካሉት ብልቶቻችን ወይም የሰውነት ክፍሎቻችን መካከል እጅግ አደገኛው አካል ወይም ብልት አንደበት ነው። አጥንት እስኪሰበር የሚያደርስን ክፋት የተሞላ መርዛማ ነገር ነው። 

“እንዲሁም አንደበት ደግሞ ትንሽ ብልት ሆኖ በታላላቅ ነገር ይመካል። እነሆ፥ ትንሽ እሳት እንዴት ያለ ትልቅ ጫካ ያቃጥላል።”— ያዕቆብ 3፥5። 

“አንደበትም እሳት ነው። አንደበት በብልቶቻችን መካከል ዓመፀኛ ዓለም ሆኖአል፤ ሥጋን ሁሉ ያሳድፋልና፥ የፍጥረትንም ሩጫ ያቃጥላል፥ በገሃነምም ይቃጠላል።”— ያዕቆብ 3፥6።


በተለይ በመፅሐፍ ቅዱሳችን ስለ አንደበት የተነገረው ቃል እጅግ አሉታዊ በሆነ መንገድ የተገለጸው ነው። ስለ አንደበት በዝርዝር በማንነቱና በባህሪው የተገለጠበት መንገድ፦
1. ትንሽ ብልት
2. በታላላቅ ነገር ይመካል
3. እሳት 
4. ዓመፀኛ አለም
5. ሥጋን የሚያሳድፍ
6. ሩጫን የሚያቃጥል
7. በገሃነምም የሚቃጠል እንደሆነ በግልፅ ተቀምጧል። 

በተለይ በነህምያ እና በዕዝራ ዘመን የፈረሰችውን እየሩሳሌምን በሚጠግኑበት ጊዜ በዙሪያቸው የነበሩት ጠላቶቻቸው የመጀመሪያውን ጦርነት የጀመሩት በአንደበት ጦርነት በሚያናንቅና በሚያጥላላ ንግግር ነው። “አሞናዊውም ጦብያ በአጠገቡ ቆሞ፦ በድንጋይ በሚሠሩት ቅጥራቸው ላይ ቀበሮ ቢመጣበት ያፈርሰዋል አለ።” — ነሀምያ 4፥3። አንደበት የዚህን ያህል ውስጥን የሚያበግን ንግግርን አፍልቆ ስሜትን ይነካል። ለዚህ ነው ነህምያ በምላሹ፦ “አምላካችን ሆይ፥ ተንቀናልና ስማ፤ ስድባቸውን በራሳቸው ላይ መልስባቸው በምርኮ አገር ለብዝበዛ አሳልፈህ ስጣቸው።” — ነሀምያ 4፥4። “በደላቸውንም አትክደን፥ ኃጢአታቸውም ከፊትህ አይደምሰስ፤ በሠራተኞች ፊት አስቆጥተውሃልና።” — ነሀምያ 4፥5። 

የአለማውያኑ ንግግር ይህን ያህል ላይጎዳ ይችላል፣ ምክንያቱም የባህሪያቸው ስለሆነ ቦታ ላንሰጠው እንችል ይሆናል። ሆኖም ግን በእኛ በክርስቲያኖች መካከል የሚደረገው የአንደበት ላይ ጦርነቶች በብዙ አኅዛብ መካከል መሳለቂያ እስከመሆን ደርሰናል። በተለይ በመፅሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ ላይ ያለን የሰፋ ልዩነትና የምንሰጣጣቸው ምላሾች በብዙዎች ዘንድ አስተችቶናል። የአንደበታችን አለመገራት በብዙዎች ዘንድ እምነታችን እንዲተችና እንዲነቀፍ መንስኤ እና ምክንያት ሆኖአል። ስለዚህ የአንደበታችንን ጉዳይ እጅግ በአፅንኦት ልንመለከተው ይገባል። በተለይ ከምናለማው በላይ የምናቃጥለው በዝቷል። 

“ነገር ግን አንደበትን ሊገራ ማንም ሰው አይችልም፤ የሚገድል መርዝ የሞላበት ወላዋይ ክፋት ነው።”— ያዕቆብ 3፥8። አንደበታችንን በራሳችን አቅም ልንገራውና ልንቆጣጠረው ባንችልም፣ እግዚአብሔር እራሱ ጠባቂ ያኑርልን። 

  1. ጉዞን ያውካል፦ ያልተጎሰመ አንደበት በሕይወት እያደረግን ያለነውን ማንኛውም ነገር የማወክ ኃይል አለው። 
    አንደበት፦ በተለይ ወሬ ከታከለበት የሌሎችን አቋም የመሸርሸርና የማውረድ አቅም አለው። “ስለ ሰለሉአትም ምድር ክፉ ወሬ ለእስራኤል ልጆች እያወሩ፦ እኛ ዞረን የሰለልናት ምድር የሚኖሩባትን ሰዎች የምትበላ ምድር ናት፤ በእርስዋም ዘንድ ያየናቸው ሰዎች ሁሉ ረጃጅም ሰዎች ናቸው።” — ዘኍልቁ 13፥32። 
  2. ከመሪ ያጣላል፦ በተለይ በአንድ ህብረት ውስጥ ያለ አንደበቱ ያልተጎሰመ አካል ሕብረቱን የማናጋትና ከመሪ ጋር የማጋጨት ብቃት አለው። ይህም ሲሆን ዓላማ እና ግብ ከስኬት እንዳይደርስ እንቅፋትና መሠናክልን ያደርጋል። “ምድሪቱንም ሊሰልሉ ሙሴ ልኮአቸው የተመለሱት ሰዎች ክፉ ወሬም ስለ ምድሪቱ እያወሩ በእርሱ ላይ ማኅበሩ ሁሉ እንዲያጕረመርሙ ያደረጉ፥”— ዘኍልቁ 14፥36። “ክፉ ወሬ ያወሩ እነዚያ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት በመቅሠፍት ሞቱ።” — ዘኍልቁ 14፥37። 

አንደበታችንን መጠቀም ያለብን መጥፎ ቃላትን ከመናገር መከልከል ብቻ ሳይሆን መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያስተምረን የሚጠቅመውን ለመናገርም ነው። በመጽሐፍም “ለሚሰሙት ጸጋን ይሰጥ ዘንድ፥ እንደሚያስፈልግ ለማነጽ የሚጠቅም ማናቸውም በጎ ቃል እንጂ ክፉ ቃል ከአፋችሁ ከቶ አይውጣ።”— ኤፌሶን 4፥29። 

ያልተጎሰመ አንደበት፦ አምልኮአችንን፣ እምነታችንን የሚያስነቅፍ፣ የሚያስተች፣ የሚያጎድፍ ነው። ስለዚህ፦ ቅዱስ ያዕቆብ ‹‹አንደበቱን ሳይገታ፥ ልቡን እያሳተ እግዚአብሔርን የሚያመልክ የሚመስለው ማንም ቢኖር፥ እርሱ አምልኮቱ ከንቱ ነው›› በማለት የተናገራቸው ቃላት ባልተገደበ አንደበት ምክንያት የአንድ ሰው የክርስትና ህይወት እና አምልኮ እንዴት ከንቱ ሊሆን እንደሚችል ያመላክታል። ክርስትና ያለ ትህትናና ምግባር ከንቱ በመሆኑ የማንተገብራቸውን ተግባራት በተዋቡ ቃላት ከሽነንና አጅበን በሽንግላ አንደበት በስመ ክርስቲያን ብቻ መኖር የተገባ አይደለም፡፡ “አንደበቱን ሳይገታ ልቡን እያሳተ እግዚአብሔርን የሚያመልክ የሚመስለው ማንም ቢኖር የእርሱ አምልኮ ከንቱ ነው።”— ያዕቆብ 1፥26። 

በሐዋርያው ያዕቆብ እንደገለጸው ከቁጥጥር ውጭ የሆነ አንደበት ወደ ኃጢአት ይመራል፡፡ አንድ ሰው ምላሱን ሳይገታ፣ በክፉ እሳቤ ተነሣስቶ ቃላትን ቢያወጣ በመንፈሳዊ ሕይወት ውስጥ እክል ይሆንበታል። አምልኮው፣ አገልግሎቱ እና ልፋቱ ሁሉ መና ይሆናል። እምነት በጎደለውና በሐሰተኛ አንደበት የእውነትን ቃላት ብናወጣ የእግዚአብሔርን ሕግ አለማክበር በመሆኑ የጽድቅ ሳይሆን የኵነኔ ፍርድ ይከተለናል፡፡ “ክፉ ወሬ ያወሩ እነዚያ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት በመቅሠፍት ሞቱ።” — ዘኍልቁ 14፥37።

በመጨረሻም፦
ስለዚህ የሰውነት አካለለችን መካከል አንደበት የማንነት መገለጫ ነው። ልንጠብቀው የሚገባ የሰውነታችን ክፍል ነው። ካልጠበቅነው ውርደታችንን የሚያፈጥን የሰውነታችን ክፍል ነው ።እግዚአብሔር የሚከብርበት እኛም የምንከብርበት ወይንም ከክብር የምንዋረድበት የሰውነታችን አካል ማለት ነው። “ሞትና ሕይወት በምላስ እጅ ናቸው፤ የሚወድዱአትም ፍሬዋን ይበላሉ።”
  — ምሳሌ 18፥21። 

“አቤቱ፥ ለአፌ ጠባቂ አኑር፥ የከንፈሮቼንም መዝጊያ ጠብቅ።” — መዝሙር 141፥3። 

“አቤቱ፥ ረድኤቴ መድኃኒቴም፥ የአፌ ቃልና የልቤ አሳብ በፊትህ ያማረ ይሁን።” — መዝሙር 19፥14። 

እግዚአብሔር ይባርካችሁ!
አገልጋይ በረከት ሱላሞ ሱጌቦ

ሥራ ፈት አንሁን

Details
Written by: Bereket Sulamo
Category: The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ

ሥራ ፈት አንሁን

ሥራ ፈትነት ከምሁራን አንደበት

ሥራ ፈትነትን ከማብራራት አስቀድሜ ነገሬን በዚህ ሥራ በሚለው ጉዳይ ላይ አንድ ምሁር የተናገሩትን ትንሽ ቁም ነገር አዘል ጉዳይ ጠቆም ላድርግና ወደ ተነሳሁበት ሃሳብ ትንሽ ቆየት ብዬ ልመለስ፡፡ ይህ ምሁር ቮልቴር የሚባል ፈረንሳዊ ሊቅና ፈላስፋ ሲሆን ስለ ሥራ የተናገረውን ላንሳ፡- ቮልቴር ሲናገርሥራ ከሶስት ነገሮች የሰውን ልጅ ይጠብቃል ብሎ ይናገራል፡፡

  1. ከድባቴ ወይም ከድብርት
  2. ከመጥፎ እኩይ ተጋባርና ድርጊት
  3.  ከድህነት፤ ከችግር ይጠብቃል ይከላከላል በማለት ሙያዊ ምክሩን ይሰጣል፡፡

እውነታው ላይ ተመርኩዘን ስናየውና ስናጤነው ቮልቴር የተናገረው እጅገ እውነት ነው፡፡ በምድራችን አሁን ላይ የምናየው የስራ ፈትነት ካመጣቸው አሉታዊ ችግሮች በይበልጥ ተስተውለው የሚታዩት እነዚህ ናቸው፡፡

ዛሬም በቤተክርስቲያን ውስጥ ከዚህ የተለየ ችግር እያየን አይደለም፡፡ ጉዳዩ የአለማዊ ዕውቀት እና የመንፈሳዊ እውቀት ብለን እንፈርጀው እንጂ በስው ልጅ ላይ እየታየ ያለው ተመሳሳይ ነገር ነው፡፡ ዛሬ ላይ መንግስታትን እያሳሰበ እና እየተፈታተን ያለው ነገር ቢኖር የሥራ ፈት ቁጥር ማሸቀቡና ለዚህም መፍትሄ ማጣቱ ነው፡፡

Read more: ሥራ ፈት አንሁን

የተገለጠው የእግዚአብሔር ጸጋ

Details
Written by: Mekete Sugebo
Category: The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ

የእግዚአብሔር ጸጋ

Read more: የተገለጠው የእግዚአብሔር ጸጋ

  1. በክርስቶስ የተገኘ ልጅነት እና ትሩፋቶቹ
  2. የምትሰማው ድምጽ
  3. የጌታ ደስታ
  4. እግዚአብሔር ከስምህ በላይ ነው

Subcategories

ከመጽሐፍት ዓለም

Page 1 of 3

  • 1
  • 2
  • 3
  • በመከራ ውስጥ የሚፀና ማንነት
  • በሚበልጥ ክብር መገለጥ
  • አልባሾችህን_ጠንቅቀህ_እወቅ
  • አልባሾችህን ጠንቅቀህ እወቅ
  • የይሁዳ መልዕክት

Article Categories

  • Literature/ስነ-ጽሑፍ
  • Gospel Thoughts / የወንጌል አስተምህሮ
  • The Feast of the Word/ከቃሉ ማዕድ
  • Testimony/ምስክርነት
  • Religious News/ሐይማኖታዊ ዜና
  • Churches/ቤተ ክርስቲያን

Login Form

  • Forgot your password?
  • Forgot your username?
Copyright © 2026 yegizewkal. All Rights Reserved.